የሀገር ውስጥ ዜና

የኢትዮጵያ የሐይማኖት ተቋማት ጉባኤ ከሃገር ውጪ የመጀመሪያውን የመመስረቻ ጉባኤ አካሄደ

By Tibebu Kebede

May 22, 2021

አዲስ አበባ ፣ ግንቦት 14 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ የሐይማኖት ተቋማት ጉባኤ የሠላም ግንባታ፣ የአብሮነትና የመከባበር የጋራ ዕሴቶችን አጠናክሮ መስራት የሚያስችለውን የመመስረቻ ጉባኤ ከሃገር ውጪ ለመጀመሪያ ጊዜ በአሜሪካ አካሄደ።

ጉባኤው የኢትዮጵያ የሐይማኖት ተቋማት ጉባኤ ዋና ጸሐፊ ሊቀ ትጉኃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ፣ የሐይማኖት ተቋማት ተወካዮች እና በአሜሪካ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ፍጹም አረጋ በተገኙበት በዋሽንግተን የኢትዮጵያ ኤምባሲ ተካሂዷል።

የሐይማኖት ተቋማት ጉባኤ ዋና ጸሐፊ ሊቀ ትጉኃን ታጋይ “ከሁሉም ቤተ እምነት ከተወከሉ የሃይማኖት አባቶች ጋር በጉዳዩ ሰፊ ውይይት ከተደረገ በኋላ ከሃገር ውጪ የመጀመሪያው የመመስረቻ ጉባኤ ተካሂዷል” ብለዋል።

በዚህም የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የጋራ ዕሴት የሆነውን የሠላም ግንባታ፣ የአብሮነትና የመከባበር ተግባራትን አጠናክሮ ለመስራት ሀገራዊና ተቋማዊ ጥንካሬ እንዲፈጠር የጉባኤው መመስረት ጉልህ አስተዋጽኦ ያበረክታል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።