የሀገር ውስጥ ዜና

አምባሳደር ዓለምፀሃይ ከኡጋንዳ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲኤታ ጋር ተወያዩ

By Tibebu Kebede

June 03, 2021

አዲስ አበባ ፣ ግንቦት 26 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በኡጋንዳ የኢትዮጵያ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ዓለምፀሃይ መሰረት ከኡጋንዳ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲኤታ ኦሪየም ኦኬሎ ተወያይተዋል።

በውይይቱ በሁለትዮሽ ግንኙነትና አካባቢያዊ ጉዳዮች ላይ መክረዋል፡፡

አምባሳደር ዓለምፀሃይ በአሁኑ ወቅት በትግራይ ክልል አስፈላጊ የሰብዓዊ ድጋፍ እና መልሶ ማቋቋም ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን፥ ከምርጫ ጋር በተያያዘም እስካሁን ከተካሄዱት ምርጫዎች የተሻለና ተዓማዓኒነት ያለው ምርጫ ለማካሄድ አስፈላጊ ቅድመ-ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆኑን ገለጻ አድርገዋል፡፡

የኡጋንዳ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲኤታ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በባለብዙ ወገን መድረኮች የነበራትን ጠንካራ ተሳትፎ በማንሳት፣ ሀገሪቱ በጊዜ ሂደት በገነባቻቸው ተቋማት ታግዛ ወቅታዊ ሁኔታዎች እና ዲፕሎማሲያዊ ፈተናዎችን በስኬት እንደምትሻገር ያላቸውን እምነት መግለፃቸው ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ፅህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

እንዲሁም ኡጋንዳ በቅርቡ ምርጫ አካሂዳ እንደነበር በማስታወስ አንዳንድ የዓለም-አቀፍ ማህበረሰብ አካላት ከአጋዥነት ይልቅ አፍራሽ እንቅስቃሴዎችን ሲያደርጉ እንደሚስተዋሉ ገልፀው ነገር ግን የአንድ ሀገር ምርጫ የሚወሰነው በዋናነት በሀገሪቱ ህዝብና በፖለቲካ ፓርቲዎች ዴሞክራሲያዊ ተሳትፎ ብቻ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!