የሀገር ውስጥ ዜና

ለጌርጌሴኖን የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማህበር 3 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ተሰጠ

By Tibebu Kebede

June 12, 2021

አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 5 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለጌርጌሴኖን የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማህበር 3 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ሰጠ።

ማህበሩ ሽሮ ሜዳ ቁስቋም አካባቢ 3 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ከከተማ አስተዳደሩ በነጻ የተረከበ ሲሆን በስፍራው ለሚገነባው የህሙማን ማገገሚያ ማዕከል ሕንጻም የመሰረት ድንጋይ ተቀምጧል።

የማህበሩ መስራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ መለሰ አየለ የማዕከሉ ሕንጻ በ2 ሺህ 500 ካሬ ሜትር ላይ የሚያርፍ ሲሆን ለግንባታውም 150 ሚሊየን ብር ወጪ ይደረጋል ብለዋል።

ማዕከሉ የራሱ የገቢ ምንጭ የሌለው በመሆኑ ለማዕከሉ ግንባታ ህብረተሰቡ የተለመደውን ትብብር እንዲያደርግም ጠይቀዋል።

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ጥራቱ በየነ ሕንጻው ተገንብቶ እስከሚያልቅ ድረስ ከተማ አስተዳደሩ ድጋፍ እንደሚያደርግ መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ጌርጌሴኖን የአዕምሮ ሕሙማን መርጃ ማህበር ከተመሰረተበት 1998 ዓ.ም ጀምሮ በርካታ የአዕምሮ ሕሙማን ከጎዳና እና ከሃይማኖት ተቋማት በር ላይ በማንሳት እየደገፈ ሲሆን፥ በአሁኑ ሰዓት ለ450 የአዕምሮ ሕሙማን አረጋውያንና የአዕምሮ እድገት ውስንነት ያለባቸው ሕጻናትን በመርዳት ላይ ይገኛል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!