የሀገር ውስጥ ዜና

ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎችን ለዘላቂ ሰላም መጠቀም ይገባል – ብጹዕ ካርዲናል ብርሃነ ኢየሱስ ሱራፌል

By Tibebu Kebede

June 14, 2021

አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 7 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮጵያ ያሉ ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎችን ዘላቂ ሰላም ለማስፈን መጠቀም እንደሚገባ የኢትዮጵያ ዕርቀ ሰላም ኮሚሽን ሰብሳቢ ብጹዕ ካርዲናል ብርሃነ ኢየሱስ ሱራፌል ጥሪ አቀረቡ።

የኢትዮጵያ እርቀ ሰላም ኮሚሽን ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር “ዘላቂ መፍትሄ በሀገር በቀል የግጭት አፈታት ዘዴዎች” በሚል መሪ ሃሳብ የምክክር መድረክ እያካሄደ ነው።

በመድረኩ ከሁሉም ክልሎች እና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ 200 የሚጠጉ የሃይማኖት አባቶች፣ የሃገር ሽማግሌዎችና ወጣቶች ተሳታፊዎች ናቸው።

መድረኩ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ወጣቶች ለሀገር ሰላም የበኩላቸውን እገዛ እንዲያደርጉ መዘጋጀቱም ተገልጿል።

በመድረኩ መክፈቻ ንግግር ያደረጉት ብጹዕ ካርዲናል ብርሃነ እየሱስ ሱራፌል ኮሚሽኑ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ የተለያዩ ተግባራትን ሲያከናውን መቆየቱን አንስተዋል።

የሌሎች ሃገራት ልምድ መቅሰም፣ ከክልል መስተዳድሮች ጋር ጥሩ የስራ ግንኙነት መፍጠር እና በክልሎች ቅርንጫፍ መክፈት ኮሚሽኑ ያከናወናቸው ተግባራት መሆናቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል።

በኢትዮጵያ በርካታ ጥቃቶችና ግጭቶች መከሰታቸውን አስታውሰው፥ ኮሚሽኑ ሁሉንም አይነት ግጭቶች ብቻውን የመፍታት አቅም እንደሌለው መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

ኢትዮጵያ በባህላዊ መንገድ ግጭቶችን በመፍታት ረገድ የዳበረ ባህል ያላቸው ህዝቦች ባለቤት መሆኗንም አውስተዋል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!