የሀገር ውስጥ ዜና

ምርጫው እጅግ ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ሆኖ መጠናቀቁ ታሪካዊ ድል ነው- የኦሮሚያ የፖለቲካፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክክር መድረክ

By Tibebu Kebede

June 27, 2021

 

አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 20፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ስድስተኛው ሃገራዊ ምርጫ እጅግ ሰላማዊና ዲሞክራሲዊ ሆኖ መጠናቀቁ ታሪካዊ ድል ነው ሲል የኦሮሚያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክክር መድረክ አስታወቀ።

ምክክር መድረኩ ዛሬ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ስድስተኛው ሃገራዊ ምርጫ ከዚህ ቀደም ከተካሄዱ ምርጫዎች እጅግ ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ሆኖ መጠናቀቁ፥ዲሞክራሲያዊ ሃገር ለመገንባት ታሪካዊ ድል ያደርገዋል ሲል ነው የገለጸው።

በኦሮሚያ ክልል የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች የተመሰረተው ይህ መድረክ ሰኔ 14 የተካሄደውን ምርጫ ከየፓርቲዎቹ የቀረቡለትን ቅሬታዎች በመለየት በወቅቱ መፍታት የሚቻሉትን እንዲፈቱ በማድረግ እንዲሁም መድረኩ መፍታት የማይችላቸውን ለሚመለከተው አካል ማሳወቁን ገልጿል።

ስድስተኛው ሃገራዊ ምርጫ ህብረተሰቡ በሰላማዊ መንገድ በነቂስ ወጥቶ ድምጹን የሰጠበት እንዲሁም ከታዩ ጥቂት ችግሮች በስተቀር ፍትሃዊ ዲሞክራሲያዊ መሆኑ ሃገሪቱ የዲሞክራሲ ስርዓትን ለመገንባት የጀመረችው ጉዞ አንድ እርምጃ ወደፊት ያራመደ መሆኑን ተናግረዋል።

ሰባት ፓርቲዎችን የያዘው ምክክር መድረኩ ፖለቲካ ፓርቲዎች ለአንድ ሃገር በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግ ገልጿል።

ፓርቲዎቹ ከአሸናፊው ፓርቲ ጋር በመሆን ለሃገር ግንባታ እና ልማት በጋራ ለመስራት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።

የጋራ መድረኩ ከዚህ በላይ ተጠናክሮ እንደሚሰራ በመግለጽ፥የኢትዮጵያ ህዝብ በምርጫው ያሳየው ጨዋነት ተነሳሽነትን አመስግኗል እንዲሁም የጸጥታ አካላቱን ጨምሮ በእለቱ ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ለነበራቸው ተሳትፎ አመስግኗል።

ሃይማኖት ኢያሱ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!