Fana: At a Speed of Life!

መንግስት የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ላቀረበው ጥያቄ ምላሽ ሰጠ

አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 21 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) መንግስት የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ክልሉ ያጋጠመውን ችግር ለመፍታት ላቀረበው የመፍትሔ ሐሳብ መንግሥት ምላሽ ሰጠ፡፡

አሸባሪው የሕወሓት ቡድን ባለፉት ሰላሳ ዓመታት በሀገሪቱ ላይ ትውልድ ገዳይ መከራ ማስከተሉ ይታወቃል፡፡ ኢትዮጵያውያን ከዳር እስከዳር ባደረጉት መራራ ትግል ይህ መከራ ተወግዷል፡፡

ያለፉ በደሎችን በይቅርታ ለመሻገር የለውጡ ኃይል አድርጎት የነበረውን ተደጋጋሚ ጥረት ማንም የሚያስታውሰው ነው፡፡ በፍቅር እንደመር፣ በይቅርታ እንሻገር በሚለው መርሐችን መሠረት፣ ሁልጊዜ እያፈረስን ከምንገነባ፣ያለፈውን በይቅርታ፣የሚመጣውን በካሣ ለማለፍ ጥረት አድርገን ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብም ለሁላችንም የመታረሚያ ዕድል ሰጥቶን ነበር፡፡

ይሁን እንጂ የሕወሐት ቡድን ኢትዮጵያን አፈራርሼ ፍርስራሹን እየሸጥኩ ካልተጓዝኩ በሚል የሕዝቡን ይቅርታ ከቁብ አልቆጠረውም፡፡ ራሱንም ከለውጥ ሂደቱ ከማውጣት አልፎ ለውጡን ለማደናቀፍ መሰናከል ማብዛት ጀመረ፡፡ በዚህ አቋሙም ተደጋጋሚ የሆኑ የመታረሚያ ዕድሎችን አበላሸ፡፡ ይባስ ብሎ ግጭቶችን እየጠነሰሰ፣ እልቂት እየደገሠ ሀገር ለማፍረስ መሥራት ቀጠለ፡፡ በኢሕአዴግ እና በመንግሥት መድረኮች ችግሩን በውይይት ለመፍታት የነበረውን ዕድል አጨናገፈው፡፡ በሀገር ሽማግሌዎች፣ በሃይማኖት አባቶች እና ሕወሐትን ከፌዴራል መንግሥት ጋር ሊያቀራርቡ ይችላሉ በተባሉ አካላት በኩል የተሞከሩ የሽምግልና ሙከራዎች ሁሉ በሕወሐት አልጠግብ ባይነት ከሸፉ፡፡

ይህ ሁሉ ቢሆንም እንኳን የከፋ ሀገራዊ ቀውስ እስካልተፈጠረ ድረስ ችግሩን በሆደ ሰፊነት ማየት ይገባል የሚል አቋም መንግሥት ነበረው፡፡ የሕወሐት ቡድን ለክልሉ የተላከውን በጀት ለጦርነት ድግስና ለጥፋት እያዋለው መሆኑ እየታወቀ ህዝቡ እንዳይጎዳ ሲባል የክልሉ በጀት ሳይቋረጥ እንዲያውም ተጨማሪ በጀት ተሰጥቶታል፤ ክልሉ በፌዴራል መንግሥት የነበረው ውክልና ሳይነካ በሰላም ለመቀጠል ተሞክሯል፡፡ በሀገሪቱ ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች ግጭትና መፈናቀል እያስከተለ እንኳን የትግራይን ክልል ከማስተዳደር ያገደው አልነበረም፡፡

ይሄንን ሁሉ የመንግሥት ትእግሥት እንደ ፍርሃት የቆጠረው የሕወሐት ቡድን በጥቅምት ወር በሰሜን ዕዝ ላይ ሀገር ሊያፈርስ የሚችል ጥቃት ፈጸመ፡፡ ከሃያ ዓመታት በላይ ድንበር ሲጠብቅና የትግራይን ሕዝብ ሲረዳ በኖረው የሰሜን ዕዝ ላይ አሰቃቂ ግፍ ሠራ፡፡ አንዳንዶችን ገደለ፤ አንዳንዶችን አረደ፤ በአንዳንዶች ላይ ኢሰብአዊ ተግባር ፈጸመ፤ ሴት ወታደሮችን አዋረደ፡፡ የሰሜን ዕዝን መሣሪያ ወስዶ በኢትዮጵያ ላይ ግልጽና ቅርብ አደጋ ደቀነ፡፡

የመከላከያ ሠራዊታችን በሕገ መንግሥቱ በተጣለበት የሀገርን ሉዓላዊነትና ህልውና የመጠበቅ ኃላፊነት መሠረት፣ በወሰደው ሕግ የማስከበር ርምጃ የሕወሐት ቡድን ከጥቅም ውጭ ሆነ፡፡ መዋቅሩ ፈረሰ፤ ወታደራዊ አቅሙ ተደመሰሰ፤ አመራሩ ምርኮኛ ሙትና ቁስለኛ ሆነ፤ የቀረውም ተበተነ፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት ሕግ የማስከበር ዘመቻ ሲከፍት ዓላማው የሕወሐትን ቡድን ከጥቅም ውጭ ማድረግና ኢትዮጵያን መታደግ ነበር፡፡ በዚህ ዓላማም ቡድኑ ከዚህ በኋላ ሀገራዊ አደጋ ከማይደቅንበት ደረጃ ወርዶ፣ የተረፈው ኃይል የተበተነ ርዝራዥ ሆኗል፡፡ አደጋ ሊያደርስበበት የነበረውን የጦር መሣሪያም ተነጥቋል፡፡ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ዐቅሙም ኢምንት ሆኗል፡፡ በአጎራባች አገሮችና ክልሎች የነበረው የጥፋት ሃይሉ ማምለጫ መንገድ በመከላከያ ሃይል ስለተዘጋ ወንጀለኞች ያሚያመልጡበት እድል ተመናምኗል። በዚህም የተነሣ ፈፋ ለፈፋ እንደ እየዘለለ የሚኖር ሽፍታ ሆኗል፡፡

የኢትዮጵያ መንግሥት ሕግ የማስከበር ዘመቻውን በዋናነት ካጠናቀቀ በኋላ ፊቱን ወደ መልሶ ግንባታ በማዞር የሕወሐት ቡድን ባደረሰው ጥፋት የወደሙትን መሠረተ ልማቶች ለመገንባት የህይወት መስዋእትነት ጭምር ተከፍሎ ሰፊ ርብርብ አድርጓል ። በግጭቱ የተጎዱ ወገኖችን ለመርዳትና አገልግሎቶች እንዲጀመሩ ለማድረግም ሰፊ ሥራ ሠርቷል፡፡ ይሄንን የርዳታና የመልሶ ግንባታ ሥራ ለማገዝ የፌዴራል መንግሥቱና የክልል መንግሥታት ከመቶ ቢሊየን ብር በላይ ወጪ አውጥተዋል፡፡

ከሰላሳ በላይ የእርዳታ ድርጅቶችና አራት መቶ የሚጠጉ ሰራተኞቻቸው ክልሉን ገብተው እንዲረዱ አድርጓል፡፡ ሌላው ቀርቶ የመገናኛ ችግር እንኳን እንዳይፈጠር በተለየ መልኩ ለዓለም አቀፍ ድርጅቶች የራሳቸው የመገናኛ መሣሪያዎችን ለመጠቀም የሚያስችል ዕድል ተፈጥሯል፡፡ ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ የሚዲያ ተቋማት ሂደቱን እንዲዘግቡ ተፈቅዷል፡፡ የቪዛና የጉዞ ፈተናዎች እንዳይኖሩ ሁኔታዎች ሁሉ ተመቻችተዋል፡፡

በዚህ ጉዞ ውስጥ ግን አንዳንድ ዓለም አቀፍ አጋሮቻችን ችግሩን ለመገንዘብ ፍላጎት አላሳዩም፡፡ ለርዳታ የከፈትንላቸውን መሥመርም ላልተገባ ተግባር ሲጠቀሙበት ታይተዋል፡፡ አንዳንድ ሚዲያዎችም ከእውነት በተቃራኒ መቆምን መርጠዋል፡፡

ከሚደርሱት ርዳታዎች ከሰባ በመቶ በላይ የሚሸፍነው የኢትዮጵያ መንግሥት መሆኑ እየታወቀ ለመንግሥት ተግባር ዕውቅና ነፍገዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንግሥት የትግራይ ሕዝብ ከሚጎዳ ጫናውን ተሸክሞ ማለፍ ይሻላል በሚል መርሕ ይሄን ሁሉ ጫና ተቋቁሞ አልፏል፡፡

የትግራይን ሕዝብ ችግር የመፍታት ቀዳሚውና ዋናው ኃላፊነት የኢትዮጵያ መንግሥት እንጂ ርዳታ ሳይሰጡ ስለ ርዳታ የሚያወሩ አካላት እንዳይደለ በማመን የተቻለውን ሁሉ አድርጓል፡፡

ከሕግ ማስከበር ዘመቻው በኋላ የነበረው ጊዜ ርዳታ ለማድረስ፣ መንግሥታዊ አገልግሎቶችን ለማስጀመር፤ የጸጥታና የፍትሕ አካላትን ለማሠልጠንና ለማሠማራት፣ መሠረተ ልማቶችን መልሶ ለመገንባት፣ ለመንግሥት ሠራተኞች ደመዝ ለመክፈል፣ ሕዝቡን አስቀድሞ ሕወሐት ካቆራረጠው ወገኑ ጋር ለማገናኘት ውሏል፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን የተበተነውን ሽፍታ አመራር ለመያዝ ባደረግነው ዘመቻ ዋና ዋናዎቹ አንድም ተደምስሰዋል፤ ወይም ተይዘዋል፡፡ የቀሩትም በሃገር ላይ አደጋ ከማድረስ አንፃር ትርጉም የሌላቸው ሆነዋል፡፡

ከላይ የተገለፀው ሁኔታ እንዳለ ሆኖ ህግ ማስከበር ሁኔታ ጎን ለጎን የክልሉን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት በኢትዮጵያውያንና በኢትዮጵያ ወዳጆች ሲቀርቡ የነበሩ የመፍትሔ ሃሳቦችን የፌደራል መንግስት ስያጤናቸው ቆይቷል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር በተካታታይ ያቀረበውን ጥያቄ መንግሥት ከተለያየ አቅጣጫ ተመልክቶታል፡፡ በአንድ በኩል አካባቢው ከሚመራ አካል የቀረበ በመሆኑ፤ በሌላ በኩል ጥያቄው ከመቅረቡ በፊት በተለያየ ጊዜ ከክልሉ ተወላጆች፣ ከሀገር ሽማግሌዎችና ከሃይማኖት አባቶች ጋር ውይይት የተደረገበት መሆኑን ከግምት ውስጥ አስገብተናል፡፡

በስድስተኛው ሃገራዊ ምርጫ የኢትዮጵያ ህዝብና ተፎካካሪ ፓርቲዎች ከመቸውም በላይ ለሃገራችን ሰላም የሰጡት ልዩ ትኩረት ከግምት ውስጥ ገብቷል፡፡ ይህንንም ሰላም የኢትዮጵያ አንዱ አካል የሆነውን የትግራይ ህዝብ ተቓዳሽ ሊሆን ይገባል ተብሎ ስለሚታመን። የትግራይም ህዝብ ሰላምና ለውጥ ፈላጊ መሆኑ በተለያዩ መንገዶች ሲገልፅ የቆየ መሆኑን ስለሚታወቅ። የሀገሪቱን ሉዓላዊነት ከውጭ ኃይሎች ከተሰነዘሩ ትንኮሳዎች ለመከላከልና ሁለተኛውን ዙር የሕዳሴ ግድብ ለመሙላት ትኩረት መስጠት የወቅቱ አንገብጋቢ ጥያቄ በመሆኑ።

የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር እንደገለጠው፣ መላው ሕዝብም እንደሚረዳው፣ የተበተነው የሕወሐት የጥፋት ኃይል በሚሽሎኮሉኩባቸው አካባቢዎች ገበሬው ተረጋግቶ ወደ እርሻ ሥራ መግባት አልቻለም፡፡

ባለፈው አመት የአምበጣ መንጋ በስፋት ያጠቃው ክልል በመሆኑ የግብርና ሰብል ምርት በበቂ ሁኔታ አላገኝም፤ ከአንበጣ የተረፈውን መሰብሰብ እንዳይችል በመሰብሰብያ ግዜው በህዝብ ስም የሚነግደው ሕወሐት አከባቢውን የግጭት ቀጣና አደረገው። በዚህ ሁኔታ ይሄንን ክረምት ያለ እርሻ ሥራ የሚያሳልፍ ከሆነ፣ ለገበሬው በዕንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ይሆንበታል፡፡ የሕወሐት የጥፋት ኃይል በሚነዛው ሽብር የተነሣ ሕዝቡ የጦርነት ጋሻ ሆኖ እየተማገደ ይገኛል፡፡ ሲዋጋ ሚሊሻ ሲጠቃ ሲቪል የሚሆን ኃይል እየተፈጠረ ነው፡፡ በዚህ የተነሣ ሕወሐት በፈጠረው ቀውስ ቤታቸው የፈረሰባቸው፣ እርሻቸው የተስተጓጎለባቸው፣ አካባቢያቸውን ለቅቀው የተፈናቀሉ ሁሉ የተረጋጋ ኑሮ ለመኖር አልቻሉም፡፡

በአንድ በኩል እነዚህን ነገሮች ከግምት ውስጥ በማስገባት፤ በሌላ በኩል ደግሞ በረሐ ከተበተነው ኃይል ውስጥ ሁኔታዎች ቢመቻቹለት ወደ ሰላም ሊመጣ የሚችል ኃይል ይኖራል ተብሎ ስለታመነ፣ የጊዜያዊ አስተዳደሩን ጥያቄ መንግሥት በአዎንታዊነት ተቀብሎታል፡፡
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ ዋነኞቹን የጥፋት መሪዎች ለህግ የማቅረብ ስራ እና የተጀመረው የምርመራ ተግባር ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል።

በዚህም መሠረት ገበሬው ተረጋግቶ የእርሻ ሥራውን እንዲከውን፣ የእርዳታ ሥራው ከወታደራዊ እንቅቃሴ ነጻ ሆኖ እንዲሠራጭ፣ ሰላምን የሚመርጡ የሕወሓት ርዝራዥ አካላት ወደ ሰላም መንገድ እንዲመጡ፤ ሳያውቁ ርዝራዡን የጥፋት ኃይል የተከተሉ እንደገና ለማሰብና ወደ ሰላማዊ መንገድ ለመምጣት ዕድል እንዲያገኙ ለማስቻል፣ ይህ የእርሻ ወቅት እስኪጠናቀቅ ድረስ የሚቆይ ያለቅድመ ሁኔታ በሰብአዊነት ላይ የተመሠረተ በተናጠል የተኩስ አቁም ከዛሬ ከሰኔ 21 ቀን 2013 ጀምሮ መንግሥት አውጇል፡፡

ሁሉም የፌዴራልና የክልል ሲቪልና ወታደራዊ ተቋማት፣ ከመንግሥት በሚሰጣቸው ዝርዝር አፈጻጸም መሠረት ይሄን የተኩስ አቁም እንዲያከብሩና እንዲያስከብሩ ታዘዋል፡፡ ይሄን መልካም ዕድል ለክፉ የሚጠቀሙ ወገኖች ካጋጠሙ ግን አስፈላጊው ሕግን የማስከበር ተግባር እንደ አግባቡ የሚከናወን ይሆናል፡፡

የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግሥት

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.