Fana: At a Speed of Life!

ቡሩንዲ የኤሌክትሪክ ኃይል ለመግዛት የታላቁ ህዳሴ ግድብን መጠናቀቅ እየጠበቀች ነው ተባለ

አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 30፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ)ቡሩንዲ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ተጠቃሚ ለመሆን የታላቁ ህዳሴ ግድብን መጠናቀቅ እየጠበቀች መሆኑ ተገለጸ።
በዩጋንዳ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር አለምጸሀይ መሰረት ከቡሩንዲ ውሃ፣ ኢነርጂ እና ማዕድን ሚኒስትር ኢነንጂነር ኢብራሂም ኡውዜይ ጋር በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብና በሁለትዩሽ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት አድርገዋል።
አምባሳደሯ የታላቁ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ የግድቡ ግንባታ እና ድርድር ያለበትን ሁኔታ በማስረዳት ግድቡ የሁለተኛ ዙር ሙሌት በተያዘለት የጊዜ ሰለዳ መሰረት የሚከናወን መሆኑን ይህም በሶስቱ ሃገራት መካከል እ.ኤ.አ 2015 በተደረገው የመርሆች መግለጫ ስምምነት መሰረት መሆኑን ገልጸዋል።
ሚኒስትሩ በበኩላቸው ካለ ሀይል አቅርቦት ልማት እና እድገት የማይታሰብ መሆኑን በመግለፅ የተፋሰሱ ሀገራት የህዝብ ብዛት ቁጥር እየጨመረ ባለበት በአሁኑ ወቅት ኤሌክትሪክ አቅርቦትም በተመጣጠነ ሁኔታ ማደግ ያለበት ቢሆንም ይህ በአብዛኛዎቹ ሃገራት መሳካት አለመቻሉን ጠቅሰዋል።
በተጨማሪም ቡሩንዲ በምሥራቅ አፍሪካ በታላላቅ ሐይቆች ውስጥ ያለች እንዲሁም የናይል ተፋሰሰ አባል ሀገር ብትሆንም የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦቷ በጣም አነስተኛ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፥ በተሻለ ዋጋና አቅርቦት ከታላቁ ህዳሴ ግድብ የኤሌክትሪክ ሀይል ለመግዛት ቡሩንዲ የግድቡን መጠናቀቅ እየተጠባበቀች እንደሆነ ገልጸዋል።
በተያያዘም ሚኒስትሩ ከፍተኛ የውሃ ሃይል የሚያመነጩ እና ምቹ መልካም ምድር ያላችው እንደ ኢትዮጵያ ያሉ አገራት እንደ ህዳሴ ግድብ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች በመገንባት ለቀጠናው በቂ የኤሌክትሪክ ሀይል በማቅረብ የኤሌክትሪክ ሃይል-መር ትስስር መፍጠር ተገቢ መሆኑን አስምረውበታል፡፡
አምባሳደሯ በበኩላቸው የህዳሴ ግድብ በኤሌክትሪክ ሀይል እጦት ለሚሰቃዩ ከ65 ሚሊየን በላይ ኢትዮጵያውያን መፍትሄ እንደሚሰጥ በመግለጽ፥ በምስራቅ አፍሪካ አገራት መካካል እየተፈጠረ ያለውን የኤሌክትሪክ ሃይል ትስስር ከማጠናከር እና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ከመፍጠር ረገድም ጉልህ ሚና እንደሚኖረው አስረድተዋል።
አምባሳደሯ ከሚኒስትሩ ጋር በነበራችው ቆይታ በሁለቱ አገራት መካከል በውሃ ልማት፣ በኢነርጂ እንዲሁም በማዕድን ዘርፍ በትብብር ለመስራት ውይይት ማድረጋቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.