ዓለምአቀፋዊ ዜና

በደቡብ አፍሪካ የተከሰተው አለመረጋጋት የታቀደና ዴሞክራሲ ላይ የተሰነዘረ ጥቃት ነው – ሲሪል ራማፎሳ

By Alemayehu Geremew

July 17, 2021

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 10፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ደቡብ አፍሪካ የተከሰተው አለመረጋጋት ቀደም ተብሎ የታቀደ እና ዴሞክራሲን ለማኮሰስ የተፈፀመ ነው ሱሉ የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ሲሪል ራማፎሳ ገለጹ።

የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ መታሰራቸውን ተከትሎ በሀገሪቱ በተነሳው አለመረጋጋት የ212 ሰዎች ህይወት ማለፉ እየተነገረ ነው።

በሁከቱ ከጠፋው የሰው ህይወት በተጨማሪ 800 ያህል ሱቆች እንደተዘረፉና በአጠቃላይ ከ1 ቢሊየን ዶላር በላይ የሚያወጣ ንብረትም መዘረፉን የኩዋዙሉ ናታል ግዛት ከንቲባ ተናግረዋል።

ራማፎሳ ብጥብጡን ተከትሎ የዙማ መኖሪያ መንደር የሚገኝበትን ኩዋዙሉ ናታል በጎበኙበት ወቅት እንደተናገሩት÷ እነዚህ ሁሉ መጠነ ሰፊ ዘረፋዎች አስቀድሞ በተደራጀ ቡድን ታቅደው የተፈፀሙ ናቸው ብለዋል፡፡

ፕሬዚዳንቱ በንግግራቸውም የተፈፀመው ስርዓት አልበኝነትና ዝርፊያ በሀገሪቷ እያደገ ያለውን ዴሞክራሲ ለማኮሰስ እንደሆነ አመላክተዋል። በቀጣይም ወንጀል ፈፃሚዎችን ለይቶ ለፍርድ የማቅረብ ስራ እንደሚከናወን ጠቁመዋል። ምንጭ፡-ቢቢሲ