የሀገር ውስጥ ዜና

ከኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት የተሰጠ ማሳስቢያ

By Tibebu Kebede

July 30, 2021

 

አዲስ አበባ ፣ሐምሌ 23፣ 2013 ( ኤፍ ቢ ሲ) የህዝባችን አንድነትና ፅናት ለመሸርሸር ጠላት እየፈበረከ የሚረጫቸውን አሉባልታዎች መከላከል ያስፈልጋል ሲል የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት አሳስቧል።

በመላው ኢትዮጵያ ህዝብ የታየው ህብረትና በአንድነት መቆም ጠላቶቻችንን አስደንግጧል ያለው መከላከያ የአሸባሪው ጁንታ ጎራ በፍርሃት እንዲርድ አድርጓል፡፡

ሆኖም የህዝባችን አንድነትና ፅናት ለመሸርሸር ጠላት እየፈበረከ የሚረጨው አሉባልታዎችን መከላከል ፣ ሳያውቁ ጠላት ሆን ብሎ የሚለቀውን አሉባልታ በመቀባበል የጠላት ወኪል የሚሆኑ ወገኖችን መምከር ፣ መገሰፅ ያስፈልጋል፡፡

በአሸባሪው ህወሓት እየተፈበረኩ በማህበራዊ ሚዲያ የሚረጩ የውሸት መረጃዎችን ፣ በየአገልግሎት መስጫዎች የሚነዙ አሉባለታዎች ፣ ስለ ሠራዊታችን የግዳጅ ውሎ ሰው የሚቀባበለው ወሬ ለጠላት ግብዓት የሚሆኑና የወገንን እንቅስቃሴን የሚጎዱ ናቸው ነው ያለው፡፡

ስለዚህ ወገኖች ሁሉ ቀጥሎ የተዘረዘሩ ጉዳዮችን በማህበራዊ ሚዲያና እርስ በርስ እንዳንቀባበል እና ሼር እንዳናደርግ እናሳስባለን፡፡

1.የመረጃ ምንጩ ያለታወቁ ቀልብ የሚስቡ መረጃዎችን ሼር ከመድረግ እንቆጠብ፤

2.የሠራዊታችን ከቦታ ቦታ እንቅስቃሴ ፣ የሚጓጓዙ የጦር መሳርያዎች አይነትና ብዛት ፣ የሎጂስቲክስ ድጋፍ እንቅስቃሴዎችን ፎቶ በማንሳት በማህበራዊ ሚዲያ አንለጥፍ ፡፡ የህን የሚፈፅም ከተመለከቱም ያስቆሙ፤ ፍቃደኛ ካልሆነ ለፀጥታ ሃይሎች ወዲያው ይጠቁሙ፡፡

3.የጠላትን ትንኮሳን የመከላከል ሥራ በማህበራዊ ሚዲያ አንለጥፍ፤

4.አንዳንድ ዩ-ቲዩበሮች ለሽርፍራፊ ሳንቲም ብላችሁ ሰበር ! ሰበር ! እያላችሁ ምንጩ ያለታወቀና ያለተረጋገጠ አሉባልታ በመንዛት የወገናችሁንና የሀገራችሁን ጥቅም አሳልፋችሁ ለጠላቶቻችን አትስጡ፤

5.ወቅታዊ ወታደራዊ እንቅስቃሴን በሚመለከት በታወቀ መንግስታዊ ወይም በሚመለከተው የመከላከያ ሃላፊ ወይም አዛዥ ያልተሰጠ መረጃ ከሆነ አንመን ፣ ሼርም አናድርግ፤

6.ሁሉም ሀገር ወዳድ ዜጋ በሰራዊታችን ግዳጅ አፈፃፀምና በህዝባችን ሞራልና ስነ-ልቦና የበላይነት ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥሩና ጠላት ሆን ብሎ የሚለቃቸውን መረጃዎች ባለማሰራጨት እንተባበር ብሏል የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት በፌስ ቡክ ገጹ፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!