የሀገር ውስጥ ዜና

ለመቄዶኒያ የበጎ አድርራጎት ማህበር ከ1 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የግንባታ ቁሳቁስ  ድጋፍ ተደረገ

By Feven Bishaw

August 02, 2021

አዲስ አበባ ፣ሐምሌ 26፣ 2013 ( ኤፍ ቢ ሲ) የገቢዎች ሚኒስቴር ለመቄዶኒያ የበጎ አድርራጎት ማህበር ከ1 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የግንባታ ቁሳቁሶች ድጋፍ አደረገ፡፡

ሚኒስቴሩ ያደረገው ድጋፍ  መቄዶኒያ የበጎ አድራጎት ማህበር ዜጎችን ከጎዳና ለማንሳት ለሚያከናውነው የማስፋፊያ ስራ የሚያግዝ ያገለገሉ የግንባታ ቁሳቁሶች መሆኑ ታውቋል፡፡

ድጋፉ ግምቱ 1 ሚሊየን 226 ሺህ 555 ብር ሲሆን በዕቃዎች ዓይነት የአልሙኒም ፓርቲሽን፣ የአልሙኒየም መስኮት፣ በሮች፣ የባኞ ቤት ዕቃዎችና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡

የገቢዎች ሚኒስትር አቶ ላቀ አያሌው በድጋፍ ርክክቡ ወቅት  “የህዝብን ሃብት ለህዝብ” እና “ለወገን ደራሽ ወገን ነው” በሚል ሃሳብ  ልዩ ልዩ ድጋፎችን መደረጉን ገልጸው ማህበሩ የዜጎችን ሸክም ለማቃለል የሚሰራ ተቋም በመሆኑ  ሚኒስቴሩ ከሚሰራው ስራ ጋር የሚደጋገፍ ስራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የመቄዶኒያ በጎ አድራጎት ማህበር መስራችና ዋና ስራ አስፈፃሚ  ዶክተር ቢኒያም በለጠ በበኩላቸው÷ ለተደረገላቸውን ድጋፍ ምስጋና አቅርበው  ድጋፉ ተጨማሪ ተረጅዎችን ለመርዳት በአዲስ አበባና በክልሎች ለሚያከናውነው የማስፋፊያ ፕሮጀክት አጋዥ መሆኑን መግለፃቸውን  ከገቢዎች ሚኒስቴር  ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡