ፋና ስብስብ

የ52 ዓመቱ ጎልማሳ በከፍታ ቦታ ላይ በተሰቀለ በርሜል ውስጥ 73 ቀናትን አሳልፏል

By Tibebu Kebede

January 29, 2020

አዲስ አበባ፣ ጥር 20፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ደቡብ አፍሪካዊው ግለሰብ ከሁለት ወራት በላይ 25 ሜትር ከፍታ ባለው እንጨት ላይ በተሰቀለ በርሜል ውስጥ በመቀመጥ ክብረወሰን አሻሽሏል።

የ52 ዓመት ጎልማሳ ቨርነን ክሩገር በከፍታ ቦታ ላይ በተሰቀለ በርሜል ውስጥ 73 ቀናትን ወደ መሬት ሳይወርድ አሳልፏል።

ግለሰቡ ከዚህ ቀደም ከ22 ዓመት በፊት 54 ቀናትን በከፍታ ቦታ ላይ በተቀመጠ በርሜል ውስጥ በማሳለፍ ክብረ ወሰን አስመዝግቦ እንደነበር ዘገባው አመላክቷል።

ይህን የቀን ቆይታውን አሁን ላይ 73 ቀን በማድረስም የራሱን ክብረ ወሰን አሻሽሎታል።

በቆይታው ምግብ እና ውሃ ከመሬት በቅርጫት እየተላከለት ሲመገብ ቆይቷል፤ በሳምንት ሁለት ጊዜ ደግሞ በጠባቧ በርሜል ውስጥ በመታጠብ ንጽህናውን ይጠብቃል።

ብዙ ነገሮችን በራሱ ማድረግ አለመቻሉና ሰዎች ላይ ጥገኛ በመሆኑ ትንሽ ተስፋ አስቆራጭ ሆኖበት እንደነበር ገልጿል።

ከዚህ ባለፈም በበርሜሉ ውስጥ ለመንቀሳቀስም ሆነ ለመተኛት እጅግ አስቸጋሪ እንደነበርም አስረድቷል።

ግለሰቡ በበርሜል ውስጥ የሚያደርገውን ቆይታ ወደ 80 ቀን የማሳደግ እቅድ እንዳለውም አስታውቋል።

ምንጭ፦ ኦዲቲ ሴንትራል