ዓለምአቀፋዊ ዜና

ሱዳን ዓለም አቀፉን የጦር ወንጀለኞች ፍርድ ቤት ለመቀላቀል የቀረበውን ረቂቅ አጸደቀች

By Alemayehu Geremew

August 04, 2021

አዲስ አበባ ፣ ሐምሌ 28 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የሱዳን የሽግግር ጊዜ አስተዳደር ካርቱም ዓለም አቀፉን የጦር ወንጀለኞች ፍርድ ቤት ለመቀላቀል የቀረበውን ረቂቅ ማጽደቁ ተሰማ።

ረቂቁ ሃገሪቱ ዓለም አቀፉን የጦር ወንጀለኞች ፍርድ ቤት ለመቀላቀል የሚያስችላትን መንገድ የሚከፍት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አብደላ ሃምዶክ በትዊተር ገጻቸው አስፍረዋል።

ይህን ተከትሎም የሃገሪቱ ሉዓላዊ ምክር ቤት የመንግስት ካቢኔ ረቂቁን ህግ አድርገው ለማጽደቅ ይወያያሉም ነው የተባለው።

ፍትህና ተጠያቂነት የህግ የበላይነትን የምናረጋግጥበት የሱዳን የጀርባ አጥንት ናቸው ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በትዊተር ገጻቸው።

የረቂቁ መጽደቅም ሱዳን የቀድሞውን ፕሬዚዳንት አልበሽርን ጨምሮ በዳርፉር ተፈጽሟል በተባለው የጦር ወንጀል የሚፈለጉ ተጠርጣሪዎችን ለዓለም አቀፉ የጦር ወንጀለኞች ፍርድ ቤት አሳልፋ ለመስጠት መቃረቧን ያመላክታል ተብሏል።

ከዳርፉር የጦር ወንጀል ጋር በተያያዘ ዓለም አቀፉ የጦር ወንጀለኞች ፍርድ ቤት ሲያየው የነበረውን መዝገብ ባለፈው ግንቦት ወር ማጠናቀቁን ቢቢሲ በዘገባው አስታውሷል።