የሀገር ውስጥ ዜና

ኢትዮጵያ ላይ እየደረሰ ያለውን የተቀናጀ ጫናን የሚያወግዝ ሰለፍ በጣሊያን ተካሄደ

By Tibebu Kebede

August 05, 2021

 

አዲስ አበባ ፣ ሐምሌ 29 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) በጣሊያን የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን አገራችን ላይ እየደረሰ ያለውን የተቀናጀ ዘርፈ ብዙ ጫና ለማውገዝ ዛሬ በጣሊያን ሮም ሰላማዊ ሰልፍ አካሂደዋል።

ሰልፈኞቹ የኢትዮጵያ ህዝብና መንግስት እንዲሁም የሀገር መከላከያ ሰራዊት እያደረገ ያለውን የአገር ህልውና የማስቀጠል ትግል ለመደገፍ ድምጻቸውን አሰምተዋል።

ሰልፉን በጣሊያን የኢትዮጵያ ኮሚኒቲ አባላት ያዘጋጁት ሲሆን ሰልፈኞቹ አሸባሪው ህወሃት በአገር እና ህዝብ ላይ እያደረሰ ያለውን ውድመት፣ እድሜ ያልደረሱ ህፃናትን በጦርነት ላይ በማሳተ የሚፈፅሙውን የጦር ወንጀል፣ የሳውዲ አረቢያ መንግስት በኢትዮጵያውያን ላይ እያደረሰ ያለውን አሳዝኝ ኢሰብዓዊ ድርጊትና የምዕራባውያን አገራትና ተቋማት እያደረጉ ያለውን ያልተገባ ጫና እንዲሁም የሚዲያዎችን የተዛባ ዜና የሚቃወሙ መፈክሮችን አሰምተዋል።

ለአገር ህልውና ከፍተኛ መስዋትነት እየከፈሉ ላሉ የመከላከያ አባላት፣ የክልሎች ልዩ ሃይል አባላትና ለሌሎች የፀጥታ አካላት ትልቅ እክብሮት እንዳላቸው እና የሀገራችንን ሉአላዊነት ለማስከበር ለሚደርጉት ትግል ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ቃል ገብተዋል።

በተመሳሳይ በሌሎችም አገራት የሚኖሩ ሁሉ የሚደረገውን ድጋፍ በመቀላቀል በአገር አድን ሂደቱ የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።

በሰልፉ ኤርትራውያን የተገኙ ሲሆን አሸባሪው ህውሃት የጦር ወንጀሎችን እየሰራ የቀጠናው ስጋት ሆኖ እያለ በምዕራባውያን ዝም መባሉ እንዳሳዘናቸው መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!