የሀገር ውስጥ ዜና

“100 ብር ለወገኔ” የሚል አገር አቀፍ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ-ግብር ሊካሄድ ነው

By Tibebu Kebede

September 02, 2021

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 27፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ‘100 ብር ለወገኔ’ የሚል አገር አቀፍ የወጣቶች ንቅናቄ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ-ግብር ሊካሄድ መሆኑን የብልጽግና ወጣቶች ሊግ ጽህፈት ቤት አስታወቀ።

የብልጽግና ፓርቲ ወጣቶች ሊግ ዋና ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ይልማ ተረፈ፤ ጉዳዩን በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫቸውም ‘100 ብር ለወገኔ’ የተሰኘ የገቢ ማሰባሰቢያ የወጣቶች ንቅናቄ እንደሚካሄድ ነው ያስታወቁት ። በአገር አቀፍ ደረጃ ከፊታችን ጳጉሜ አንድ ቀን ጀምሮ በተከታታይ ለአስር ቀናት በሚካሄደው ንቅናቄ 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ወጣቶችን በማሳተፍና 180 ሚሊዮን ብር ለመሰብሰብ ነው የታቀደው።

ገቢውበግንባር ላይ ሃገራቸውን ከአሸባሪው ህወሓት በመከላከል ላይ ላሉ ጅግኖችና አሸባሪው ቡድን በተለያዩ አካባቢዎች ባደረሰው ጥቃት ለተፈናቀሉ ወገኖች እንደሚውል ተናግረዋል።

አሸባሪው ህወሓት ወረራ የከፈተው ለመንግሥት ካለው ጥላቻ ሳይሆን አገርን ለማፈራረስ ካለው ፍላጎት የመነጨ መሆኑንም አቶ ይልማ አስረድተዋል።

በአሸባሪው የጭካኔ ተግባር ኢትዮጵያውያን ቁጭት አድሮባቸው ለአገራቸው ህልውና በአንድነት እንዲቆሙ ያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል።

” የአሸባሪ ሃይል ፀቡ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ወይንም በስም ከሚጠራቸው የአማራ ክልል መሪዎች ጋር ሳይሆን ፀቡ ከኢትዮያ ጋር፣ፀቡ ከአማራ ህዝብ ጋር፣ፀቡ ከመላው ኢትዮጵያውያን ጋር መሆኑን በተግባር እያሳዬን ነው።” ብለዋል።

ለዚህም ወጣቱ የአገሪቱ ዜጋ ከጫፍ እስከ ጫፍ እንዲነሳና የቻለ የፀጥታውን መዋቅር ተቀላቅሎ እየተዋጋ፣ ያልቻለው ደግሞ ድጋፍ በማሰባሰብና አካባቢውን በመጠበቅ ረገድ ትልቅ ስራ እየሰራ መሆኑን መግለጻቸውን የኢዜአ ዘገባ ያመለክታል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!