የሀገር ውስጥ ዜና

ኢትዮጵያ የገጠማትን ወቅታዊ ችግር ለመፍታት የምታደርገው ጥረት የሚደነቅ ነው-የጃፓን አምባሳደር

By Alemayehu Geremew

September 08, 2021

አዲስ አበባ፣ ጳጉሜን 3፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ኢቶ ታካኮ÷ ኢትዮጵያ የገጠማትን ወቅታዊ ችግር ለመፍታት የምታደርገውን ጥረት አድንቀዋል፡፡

አምባሳደሯ የኢትዮጵያ የልማት ጉዞ ፈጣን እንደሆነ ገልፀው፣ ከጃፓን ጋር እና ከሌሎች ሀገራት ጋር ያላት ግንኙነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየዳበረ መምጣቱንም አድንቀዋል፡፡

የሀገርን ሉዓላዊነት የማስከበር ሂደቱ ሀገሪቷ ከገጠማት ወቅታዊ ሁኔታ አንፃር የዜጎችን ደህንነት ለመጠበቅ መሆኑን ተገንዝበናል ሲሉም ገልጸዋል።

የተለያዩ ችግሮች በማደግ ላይ ያሉትን ሆነ ያደጉት ሀገራትን ሊያጋጥም እንደሚችል ጠቅሰው፣ኢትዮጵያ አሁን የገጠማትን ፈተና ታልፈዋለች ብለዋል።

ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ችግሮች ሁሉ ተወግደው አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የልማት፣ የፍቅርና አንድነት እንዲሆን መልካም ምኞታቸውንም ገልጸዋል።

በአዲሱ ዓመት በአዲስ መንፈስ ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲው መስክ ግንኙነቷን ይበልጥ የምታጠናክረበት እንደሚሆንም እምነቴ የፀና ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

የኢትዮጵያና ጃፓን የትብብር ግንኙነት ከ90 ዓመታት በላይ የዘለቀና አሁንም በጠንካራ ወዳጅነት የቀጠለ መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ።