አዲስ አበባ፣ መስከረም 1፣ 2014 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የጎንደር ዲስትሪክት እና የአማራ ክልል ኤሌክትሪክ አገልግሎት ሰራተኞች በጦርነቱ ከተለያዩ ቦታዎች ተፈናቅለው በደባርቅ ከተማ ከሚገኙ ተፈናቃዮች ጋር አዲስ ዓመትን አከበሩ።
የዲስትሪክቱ ሠራተኞች ለምግብነት የሚያገለግሉ 450 ሺህ ብር የሚገመት እና የአማራ ክልል ኤሌክትሪክ አገልግሎት ሰራተኞች 400 ሺህ ብር በላይ የሚገመቱ አልባሳትን ለተፈናቃዮች በመለገስ በዓሉን እንዳከበሩ የዲስትሪክቱ ዳይሬክተር አቶ ሞገስ አበራ ገልፀዋል።
የተደረገውን ድጋፍ በቦታው ተገኝተው የተረከቡት የሰሜን ጎንደር ዞን አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የቤቶች ልማት እና ኮንስትራክሽን መምሪያ ሀላፊዋ ወይዘሮ ደብረወርቅ ይግዛው በዞኑ ከ75 እስከ 100 ሺህ የሚደርሱ ተፈናቃዮች መኖራቸውን ገልጸዋል።
የተደረገው ድጋፍም ለተፈናቃዮቹ ትልቅ ዋጋ እንዳለው አስታውቀዋል።
ሀላፊዋ የተቋሙን ሰራተኞች ካደረጉት ድጋፍ በላይ አዲሱን አመት ቤታቸውን ትተው ከተፈናቃዮች ጋር ማሳለፋቸው ለተፈናቃዮቹ ትልቅ ትርጉም አለው ብለዋል።
የተቋሙ ሰራተኞች ቦታው ድረስ ተገኝተው ይህንን ተግባር በመፈፀማቸው ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል።
ተፈናቃዮቹ በበኩላቸው አዲስ አመትን በዚህ መልኩ አብረዋቸው ያከበሩትን የተቋሙን ሰራተኞች አመስግነዋል።
የተቋሙ ሰራተኞች ከዚህ በፊት በዓመት የሚከፈል ሙሉ ደሞዛቸውን ለሀገር መከላከያ ሰራዊት የለገሱ ሲሆን፥ ለተፈናቃዮቹ የተደረገው ድጋፍ ተጨማሪ መዋጮ እንደሆነ ታውቋል።
በኤሊያስ አንሙት
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!