የሀገር ውስጥ ዜና

በሰዶማ አካባቢ ለተፈናቀሉ ወገኖች ከ4 ሚሊየን ብር በላይ ድጋፍ ተደረገ

By Meseret Awoke

September 12, 2021

አዲስ አበባ፣ መስከረም 2፣ 2014(ኤፍ ቢ ሲ)በሰዶማ አካባቢ በህልውና ማስከበር ዘመቻ ወቅት ለተፈናቀሉ ወገኖች ከ4ሚሊየን 170 ሺህ ብር በላይ ድጋፍ ተደርጓል፡፡

በህልውና ዘመቻው ወቅት ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉና በሰሜን ወሎ ዞን ሀብሩ ወረዳ ድሬ ሮቃ ቀበሌ ለሚገኙ ተጎጂ አርሶአደሮች የተለያዩ የምግብ ድጋፍ ተደርጎላቸዋል።

ድጋፉን በኮምቦልቻ ከተማ አስተባባሪነት ቢላል መረዳጃና እድር ከኮምቦልቻ ፣ በአዲስ አበባ የሚገኙ የወሎና አካባቢዋ ተወላጅ ባለሀብቶች፣ የደሴ ከተማ ህዝባዊ መጅሊስ፣ በሳኡዲ አረቢያ የሚገኙ የወሎ ተወላጅ ሙስሊምች ማህበር፣ የሃርቡና የደጋን ከተሞች ነዋሪዎች አጠቃላይ ግምቱ ከ4 ሚሊየን 170 ሺህ ብር በላይ የሆነ ቁሳቁስ ድጋፍ ተደረገ።

በድጋፉ ላይ የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ዶክተር ኢንጂነር ከማል መሃመድ ደሬ ሮቃ ሶዶማዎች የጅንታውን ቅስም የሰበሩ ጀግኖች መሆናቸውን ገልጸው÷ ከየአካባቢው ተፈናቅለው በደሴና ኮምቦልቻ ከተጠለሉት በተጨማሪ በቀበሌው ውስጥ በርካታ ህዝብ በመኖሩ መታገዝ አለባቸው ብለዋል።

ድጋፍ የሚያደርጉ አካላትም ክፍተትን የለየ እንዲሆን አሳስበው÷ ለተደረገው ድጋፍ እንዲሳካ ለተጉ በሙሉ ምስጋና አቅርበዋል።

ድጋፉንም ለማህበረሰቡ ተወካይ ሼህ ሀሰን ከረሙ አስረክበዋል።

የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ዶክተር ኢንጂነር ከማል ጦርነቱ በመላው ኢትዮጵያዊያን ላይ የተከፈተ መሆኑን አውስተው÷ ኢትዮጵያ ዳግም ወደቀደመ ክብሯ ትመለሳለች ነው ያሉት።

በዘሩ ከፈለኝ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!