የሀገር ውስጥ ዜና

“በሀገሪቱ ጤናማና ጠንካራ ኢኮኖሚ መገንባት የአዲሱ መንግሥት ቀዳሚ ትኩረት ይሆናል” – ዶ/ር ነመራ ገበየሁ

By Alemayehu Geremew

September 17, 2021

አዲስ አበባ፣ መስከረም 7 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በሀገሪቱ ጤናማና ጠንካራ ኢኮኖሚ መገንባት የአዲሱ መንግሥት ቀዳሚ ትኩረት መሆኑን የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ፕላንና ልማት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ዶ/ር ነመራ ገበየሁ አስታወቁ፡፡

ዶ/ር ነመራ÷ መስከረም 24 የሚመሰረተው መንግስት ባለፉት 3 ዓመታት በሀገሪቱ ፈርጀ ብዙ ለውጦችን አስመዘግቧል ብለዋል፡፡ አሁንም በሀገሪቱ ጠንካራና ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደርግ ኢኮኖሚ ለመገንባት የተለያዩ ተጨማሪ የኢኮኖሚ ሪፎርሞችን ቀርጾ ተግባራዊ ለማድረግ እንቅስቃሴ ላይ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡

ዶ/ር ነመራ÷ የታለመውን ጠንካራ ኢኮኖሚ የሚያፋጥኑና ለሥራ አጥ ወጣቶች በርካታ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ የተለያዩ ሜጋ ፕሮጀክቶች ግንባታዎች መጀመራቸውንም ተናግረዋል፡፡

በቀጣይ ፕሮጀክቶቹን ከማጠናቀቅ ጎን ለጎን ኅብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ ለኢኮኖሚው እድገቱ ማነቆ የሆነውን የኑሮ ውድነት ለመቅረፍ እንደሚሰራና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ተገቢው ትኩረት እንደሚሰጥ አመልክተዋል፡፡

መንግሥት የውጭ ምንዛሪ እጥረት ለመፍታት ባደረገው እንቅስቃሴ በተለይ ወደ ውጭ ለሚላኩ ሸቀጦች ሰፊ ትኩረት በመስጠቱ ባለፈው ዓመት ከፍተኛ ውጤት መመዝገቡን ነው ያስገነዘቡት፡፡

በዘንድሮ ዓመትም የተመዘገበውን ውጤት ይበልጥ ከማስቀጠል በተጨማሪ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት የመሳብና በማኑፋክቸሪግ ኢንዱስትሪ ያለውን ዕድል አሟጦ ለመጠቀም በርካታ ሥራዎች መታቀዳቸውንም ከኢፕድ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡