የሀገር ውስጥ ዜና

ኢትዮጵያ የምትከተለውን የኢንዱስትሪ ልማት ፖሊሲ ተረድቻለሁ – የሩሲያ አምባሳደር

By Alemayehu Geremew

September 20, 2021

አዲስ አበባ፣ መስከረም 10፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በዛሬው ዕለት በኢትዮጵያ የሩሲያ አምባሳደር ኢቫንጂኒ ቴርኪሂን እንዲሁም የኤምባሲው የመጀመሪያ ሴክሬተሪ አሌክሲ ቼስኖኮቭ በቦሌ ለሚ እና ቂሊንጦ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ጉብኝት አካሄዱ፡፡

ጉብኝቱ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ዳንኤል ተሬሳ በተገኙበት የተካሄደ ሲሆን÷ አምባሳደሮቹ በፓርኮቹ የሚገኙ የተለያዩ ፋብሪካዎችን ጎብኝተዋል፡፡

በወቅቱም የሩሲያ አምባሳደር ኢቫንጂኒ ቴርኪሂን ÷ “ዛሬ በአዲስ አበባ ዙሪያ የሚገኙ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ለመጎብኘት ዕድል በማግኘቴ በሀገሪቷ እየተካሄዱ ስላሉት የኢንዱስትሪ ልማቶች እና ሀገሪቷ የምትከተለውን የኢንዱስትሪ ልማት ፖሊሲ በመረዳት የተሻለ ግንዛቤ አግኝቻለሁ” ብለዋል፡፡

አምባሳደሩ ሩሲያ ከኢትዮጵያ ጋር በምታደርጋቸው የኢንቨስትመንት ትስስሮች እና አማራጮች ላይ ከምክትል ኮሚሽነር ዳንኤል እንዲሁም ከፓርኩ አመራሮች ጋር ሰፊ ወይይት ማካሄዳቸውን ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።