የሀገር ውስጥ ዜና

የጅማ ዞን የመንግስት ሠራተኞች እና ወጣቶች የ “ነጩ ፖስታ ለነጩ ቤተ መንግስት” ንቅናቄ ተቀላቀሉ

By Alemayehu Geremew

September 21, 2021

አዲስ አበባ፣ መስከረም 11፣ 2014ኤፍ ቢ ሲ) የጅማ ዞን መንግስት ሠራተኞች እና ወጣቶች “ነጩ ፖስታ ለነጩ ቤተ መንግስት” በሚል በተዘጋጀው ንቅናቄ ላይ ተሳታፊ መሆናቸው ተገለጸ፡፡

በፊርማ ማኖር ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የመንግስት ሠራተኞች፣ ወጣቶች እና ባለድርሻ አካላት በተዘጋጀው ወረቀት ላይ ፊርማቸውን ሲያኖሩ÷ ኢትዮጵያ የያዘችውን እውነት የዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ማወቅ እንዳለበት ገልጸዋል፡፡

የጅማ ዞን አስተዳደር አብዱል ሀኪም ሙሉ÷ በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያን ለማፍረስና ለማዳከም የውጪ እና የውስጥ አካላት በጥምረት እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡

ይህንም እውነት ለዓለምአቀፉ ማሕበረሰብ ለማስገንዘብ በትኩረት መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡

የጅማ ዞን ወጣቶች ሊግ ኃላፊ ወጣት ድማሙ ንጋቱ በበኩሉ÷ የኢትዮጵያን እውነት ለዓለም ዓቀፉ ማሕበረሰብ በማሳወቅ ረገድ ወጣቶች ከፍተኛ ሚና መጫወት እንዳለባቸው መግለፁን ከጅማ ኮሙኒኬሽን ጽህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡