Fana: At a Speed of Life!

የሱዳን ሽግግር እንዲሳካ ኢትዮጵያ ስታራምደው የነበረውን አቋም አጠናክራ ትቀጥላለች

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 18፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ሳምንታዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫቸውም በሱዳን ወቅታዊ ሁኔታ እና በኢትዮጵያ በሳምንቱ የተከናወኑ የዲፕሎማሲ ስራዎችን በተመለከተ አንስተዋል።

ከሱዳን ጋር በተያያዘ በሰጡት መግለጫም ሱዳናውያን የውስጥ ችግራቸውን ያለ ውጭ ጣልቃ ገብነት ሊፈቱ እንደሚገባ አውስተዋል።

ኢትዮጵያም የሱዳን ሽግግር የተሳካ እንዲሆን ከዚህ ቀደም ስታራምድ የነበረውን አቋም አጠናክራ እንደምትቀጥል አስረድተዋል።

በተያያዘም የሱዳን ህዝብ በራሱ ጥበብ ለችግሩ መፍትሄ እንደሚያስገኝ እና የውጭ ጣልቃ ገብነት እንደማያስፈልግ እንዲሁም በሽግግር ሂደቱ የተፈረመውን ሰነድ መሰረት በማድረግ ዴሞክራሲያዊ ሂደቱ እንዳይደናቀፍ ጥሪ የሚያደርግ መግለጫ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት እና በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መሰጠቱን ጠቅሰዋል።

ከዲፕሎማሲ ጋር በተያያዘም የአውሮፓ ህብረት ከፍተኛ የስራ ሀላፊ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ጋር መወያየታቸውን ጠቁመዋል።

በዚህ ወቅትም የአውሮፓ ህብረት ከትግራይ ክልል ጋር በተያያዘ በኢትዮጵያ በኩል እየተሰሩ ላሉ ስራዎች የሚያሳየውን እውቅና የመስጠት ችግር ሊያስተካክል እንደሚገባ አቶ ደመቀ ማንሳታቸውን ቃል አቀባዩ ገልጸዋል።

ከኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ አኳያ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ከፈረንጆቹ 2018 ጀምሮ በኢትዮጵያ በብረታብረት ኢንቨስትመንት ዘርፍ ከተሰማራው EKOS STEEL MLL P.L.C ከተሰኘ የደቡብ ኮሪያ ኩባንያ የስራ ኃላፊ ጋር ውይይት አድርገዋል።

በጅቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደር ብርሀኑ ጸጋዬ 40 ሺህ ችግኞችን ለጅቡቲ የግብርና ሚኒስትር መሀመድ አህመድ አዋሊ አስረክበዋል።

በለይኩን አለም ፤ ተጨማሪ መረጃ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.