በሩብ ዓመቱ ከ6 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የመሰረተ ልማት እና የኃይል ስርቆት ተፈጽሟል
አዲስ አበባ፣ህዳር 2፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በ2014 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ከ6 ነጥብ 7 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የመሰረተ ልማት እና የኃይል ስርቆት መፈፀሙን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስታወቀ።
በአገልግሎቱ የህግ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አበበ ተስፉ፥ በተዘረጉ መሠረተ ልማቶች ላይ እየደረሱ ያሉ ስርቆቶች ተቋሙን ለኪሳራ ተጠቃሚውን ደግሞ ለጉዳት እየዳረጉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
አሁን ላይ በአገሪቱ የተከሰተውን የፖለቲካ አለመረጋጋት እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በመሠረተ ልማቶች ላይ የሚደርስ ስርቆት መበራከቱንም ተናግረዋል።
ስርቆቶቹ በመላ አገሪቱ የሚፈፀሙ ቢሆንም አብዛኛው በአዲስ አበባ ከተማ የሚከናወን መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ከተፈጸመው ስርቆት ውስጥ 21ዱ በአዲስ አበባ መፈፀማቸውን የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ዘግቧል።