የሀገር ውስጥ ዜና

የሰነድ ማረጋገጫ ማህተም አሰራር ተቀየረ

By Meseret Awoke

November 22, 2021

አዲስ አበባ፣ ህዳር 13፣ 2014(ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የወሳኝ ኩነት ምዝገባ እና መረጃ ኤጀንሲ የልደት፣ የጋብቻ ፣ የፍቺ ፣ የያላገባ እንዲሁም ሌሎች ማስረጃዎች አገልግሎት ሲሰጥበት የነበረውን የማረጋገጫ አሰራር መቀየሩን አስታውቋል፡፡

ኤጀንሲው እየተበራከተ የመጣውን ሰነድ አስመስሎ የመስራት ወንጀል ለመቀነስ አሰራሩን መቀየሩን ነው የገለጸው፡፡

ወንጀሉ እያደረሰ ያለውን ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ጉዳት ለመቀነስ ከዚህ ቀደም የነበረውን የሰነድ ማረጋገጫ አሰራር በዘመናዊ አሰራር በመተካት የበኩሉን ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ኤጀንሲው አስታውቋል።

ተቋሙ በዋና መስሪያ ቤት የሚሰጠውን ለፖስፖርት አገልግሎት፣ ለውጭ አገራት የቪዛ ጥያቄ ፣ ለተለያዩ የውጭ እና የአገር ውስጥ ጉዳዮች የሚውሉ ማስረጃዎች የሚረጋገጥበትን የቀድሞ የማህተም አሰራር በማስቀረት በውጭ አገር አሰርቶ ባስገባው ዘመናዊ የሆሎግራም ማረጋገጫ አሰራር ከዛሬ ጀምሮ በመተካት ተግባራዊ ያደርጋል ተብሏል።

አሰራሩ ከፖስፖርት እና ከውጭ ጉዳዮች ጋር ተያይዞ በየቦታው ተመሳስሎ በመስራት ለማለፍ የሚሞከሩ ሌብነቶች ለመግታት እገዛ የሚያደርግ እንደሚሆንም ታምኖበታል።

በተያዘው በጀት ተቋሙ የሚሰጣቸውን ሰርተፍኬቶች የደህንነት ደረጃ ከፍ ለማድረግ አዲስ የ’Personalization’ ቴክኖሎጂ ባላቸው ፕሪንተሮች ለመተካት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ ኤጀንሲው መግለጹን ከከተማው ፕሬስ ሴክሬታሪ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል ።

አካባቢዎን ይጠብቁ! ወደ ግንባር ይዝመቱ! መከላከያን ይደግፉ!

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!