Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

ቱርክ በሰሜን ሶሪያ ባካሄደችው ወታደራዊ ዘመቻ 300 ሺህ ዜጎች ተፈናቅለዋል

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 6፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) ቱርክ በሰሜን ሶሪያ እያካሄደች ባለው ወታደራዊ ዘመቻ 300 ሺህ ዜጎች ከመኖሪያ ቀያቸው ተፈናቅለዋል።

ቱርክ ባሳለፍነው ሳምንት በሰሜን ሶሪያ የሚንቀሳቀሱ የኩርድ አማጺያንን ከቀጠናው ለማስወገድ የሚያስችል ወታደራዊ ዘመቻ መጀመሯ ይታወቃል።

እየተካሄደ ባለው ወታደራዊ ዘመቻ ምክንያትም በርካታ ቁጥር ያላቸው የአካባቢው ነዋሪዎች መኖሪያ ቀያቸውን ለቀው ወደ ሌላ አካባቢ እየተሰደዱ መሆናቸው ተገልጿል።

በአካባቢው ያለውን ሁኔታ የሚከታተለው የሶሪያ ሰብዓዊ መብት ተቋም እንዳስታወቀው ቱርክ በቀጠናው እየፈጸመች ባለው ጥቃት እስካሁን 300 ሺህ ዜጎች ከመኖሪያ ቀያቸው ተፈናቅለዋል።

ይህን ተከትሎም የተለያዩ ሀገራት አንካራ በቀጠናው እየፈጸመችው ያለውን ጥቃት እንድታቆም እያሳሰቡ ይገኛሉ።

በአንፃሩ ቱርክ በአካባቢው ያለውን ቀውስ በዘላቂነት ለመቆጣጠር በቀጠናው የሚንቀሳቀሱ አማጺያንን ለአንድኔና ለመጨረሻ ጊዜ ለማስወገድ ቁርጠኛ አቋም መያዟን አስታውቃለች።

ምንጭ ፦ presstv.com

Exit mobile version