አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 1፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የሶማሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ከተሾሙ 40 ቀናት ያህል ያስቆጠሩት ሀምዛ አብዲ ባሬ ያቀረቧቸውን 26 የካቢኔ አባላት ሹመት የሀገሪቱ ፓርላማ አጽድቋል።
ካቢኔው የአልሸባብ የቀድሞ ምክትል መሪ ሙክታር ሮቦው አቡ ማንሱርንም ማካተቱን ሲ ጂ ቲ ኤን ዘግቧል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲሾሙላቸው የጠየቁትን 26 የካቢኔ አባላት ያቀረቡት ከሀገሪቷ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ መሀሙድ ጋር በመምከር መሆኑን ቀደም ሲል ጠቁመው ነበር።
ሹመቱ የጸደቀው የሀገሪቷ ፕሬዚዳንት የሆኑት ሀሰን ሼክ መሀሙድ ÷ የድርቅ አደጋን ለመግታት፣ የደኅንነት ሥጋትን ለመቅረፍ፣ የሀገሪቷን ኢኮኖሚያዊ ልማት ለማረጋገጥ እና ለሶማሊያ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለማመቻቸት ያቀረቡትን አጀንዳ መፈጸም እንዲቻል ይሠራሉ ተብሎ ዕምነት ተጥሎባቸው ነው ተብሏል፡፡
ለሹመት የቀረቡት የካቢኔ አባላት የትምህርት ደረጃ እና የሥራ ልምድ ከግምት ውስጥ መግባቱም ተመላክቷል፡፡
ሶማሊያውያን ከአዲሱ መንግስት ጋር እንዲተባበሩ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጠይቀዋል።
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!