Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

የኢትዮ-ጂቡቲ ባቡር ትራንስፖርት ባለፉት አምሥት ወራት 2 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር ገቢ አገኘ

አዲስ አበባ፣ ጥር 1፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮ-ጂቡቲ ባቡር ትራንስፖርት አክሲዮን ማኅበር ባለፉት አምስት ወራት 2 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር ገቢ ማግኘቱን አስታወቀ።

የአክሲዮን ማኅበሩ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር አብዲ ዘነበ ÷ የኢትዮ-ጂቡቲ ባቡር ትራንስፖርት የሚሰጠውን አገልግሎት እያሰፋ እንደሚገኝም መግለጻቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ባለፉት አምስት ወራት ብቻ ከ500 ሺህ ቶን በላይ ጭነት በማጓጓዝ 2 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር ገቢ ማግኘቱንም ጠቅሰዋል፡፡

ይህም ከ2014 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ወደ 600 ሚሊየን ብር ብልጫ አለው ነው ያሉት።

ማኅበሩ ካጓጓዘው ጭነት አንጻር በ2015 በጀት ዓመት ባለፉት አምስት ወራት በወጪና ገቢ ንግድ ያደረገው አስተዋጽኦ 15 በመቶ መድረሱንም ገልጸዋል፡፡

ይህም ቀደም ሲል ከነበረው 11 ነጥብ 2 በመቶ ጋር ሲነጻጸር ዕድገት እያሳየ መሆኑን አብራርተዋል።

የኢትዮ-ጂቡቲ ባቡር ትራንስፖርት አክሲዮን ማኅበር በወጪና ገቢ ንግድ የሚሰጣቸው አገልግሎቶች በዓይነትና በመጠን እያሰፋ መሄድ ለመጣው ዕድገት ማሳያ መሆኑንም አንስተዋል።

እስካሁን አገልግሎት ባልጀመረበት የሰበታ መስመርም በቅርቡ ሥራ ለማስጀመር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ተገልጿል።

 

Exit mobile version