Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

አውቶቡሶችን ለማምረት የሚያስችል ስምምነት ተፈረመ

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 11፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮ ኢንጂነሪንግ ግሩፕ 2 ሺህ የከተማ አውቶቡሶችን ለማምረት የሚያስችለውን ስምምነት ከቻይናው ዮቶንግ ኩባንያ ጋር ተፈራረመ።

በስሩ ዘጠኝ ኢንዱስትሪዎች የሚገኝበት ኢትዮ ኢንጂነሪንግ ግሩፕ በቢሾፍቱ አውቶሞቲቭ ማምረቻ ኢንዱስትሪ የከተማ አውቶቡሶችን ለማምረት የሚያስችለውን ስምምነት ነው ከቻይናው ዮቶንግ ኩባንያ ጋር ያከናወነው፡፡

ኢንዱስትሪው በአዲስ አበባ ከተማ የሚንቀሳቀሱትን የፐብሊክ ሰርቪስ ፣ሸገር እና አንበሳ የህዝብ አውቶቡሶችን ጨምሮ የተለያዩ ሞዴል ያላቸው ለቤትና ለቢሮ አገልግሎት የሚውሉ አውቶሞቢሎችን የሚያመርት ነው።

ስምምነቱ ግብዓቶችን በሀገር ውስጥ መተካት የመሚያስችል የቴክኖሎጂ ስምምነት ከመሆኑም በላይ የኢንዱስትሪውን የማምረት አቅም የሚጨምሩ ቁሳቁሶችን ያካተተ ነው ተብሏል።

አውቶቡሶቹ 40 መቀመጫ ያላቸውና ከ100 እስከ 120 ተሳፋሪዎችን የመጫን አቅም ያላቸው እንዲሁም ለኢትዮጵያ አየር ንብረት ተስማሚ ተደርገው የሚሰሩ መሆናቸው ተመላክቷል፡፡

ስምምነቱን የኢትዮ ኢንጂነሪንግ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አምባሳደር ሱሌይማን ደደፎ እና የዮቶንግ ኩባንያ በኢትዮጵያ ዋና ተወካይ ሉ ሻይ ተፈራርመዋል፡፡

በበረከት ተካልኝ

Exit mobile version