Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ርስቱ ይርዳው ለመላው የሲዳማ ህዝብ የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክት አስተላለፉ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 11፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ርስቱ ይርዳው ለመላው የሲዳማ ህዝብ የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በመልዕክታቸው እንደገለጹት የሲዳማ ህዝብ እራስን በራስ የማስተዳደር የረጅም ዘመናት ጥያቄ በህገ መንግስቱ መሠረት ምላሽ አግኝቷል፡፡

የሲዳማ ህዝብ ከሌሎች የክልሉ ህዝቦች ጋር በጋራ ተቻችሎና ተግባብቶ የኖረ ደማቅ ታሪክ ያለው ህዝብ ነው ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ቀደም ሲል የነበረው አንድነት መተሳሰብና አብሮነት የሚቀጥል ይሆናል ብለዋል፡፡

ክልል ለአስተዳደራዊ ስራ የሚያገለግል እንጂ በህዝቦች መካከል ድንበር ማኖር እንዳልሆነ የተናገሩት አቶ እርስቱ የህዝቡ የቆየ መቻቻል እና እርስ በርስ መደጋገፍ ከምን ጊዜውም በላይ ልቆ እንዲጠነክር ምኞታቸውን ገልጸዋል፡፡

የደቡብ ብሄሮች ብሄረሰቦችና ህዝቦች ክልል ከአዲሱ የሲዳማ ክልል ጋር በመቀናጀት ለጋራ እድገትና ተጠቃሚነት ጠንክሮ በመስራት የሀገራችንን እድገት ወደ ላቀ ምዕራፍ ለማሸጋገር እንተጋለን ብለዋል፡፡

ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ለመላው የሲዳማ ህዝብ እንኳን ደስ ያላችሁ በማለት መልዕክታቸውን ማስተላለፋቸውን ከክልሉ የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

Exit mobile version