አዲስ አበባ ፣ታህሳስ 27 ፣2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የወባ በሽታን እስከ ፈረንጆቹ 2030 ድረስ ሙሉ በሙሉ ለማጥፋት ብሔራዊ ወባን የማጥፋት ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን ተገለፀ።
የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጄ ዱጉማ ባለፉት ዓመታት የወባ በሽታን መከላከልና መቆጣጠር ዙሪያ በኢትዮጵያ አመርቂ ውጤቶች የተመዘገበ መሆኑን ጠቅሰዋል።
በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ በሽታውን ለማጥፋት የሚደረገዉ እንቅስቃሴ አካል በመሆን የወባ በሽታን እ.ኤ.አ በ2030 ሙሉ በሙሉ ለማጥፋት ብሔራዊ ወባን የማጥፋት ፍኖተካርታ ተዘጋጅቶ በስድስት ክልሎች፣ 12 ዞኖችና 239 ወረዳዎች ወደ ስራ መግባትቱንና እንቅስቀሴ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ይሁን እንጂ በተለይ ከኮቪድ 19 ወረርሽኝ መከሰት ጋር ተያይዞ በተከሰቱና በሌሎችም አንዳንድ ችግሮች ምክንያት የወባ ማጥፋት መለኪያዎች አፈጻጸም ውጤት በሚጠበቀው ደረጃ እየተተገበረ አለመሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ከወባ ማስወገድ ጋር በተያያዘ የሚታዩ ጠንካራ ጎኖች እንዲሁም ችግሮች ላይ በመመስረት በቀጣይ ስድስት ወራት ትኩረት ተሰጥቶ መከናወን ያለባቸውን ተግባራት ላይ የስራ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡
የወባ ማስወገድ የአፈፃፀም ግምገማ በአዳማ ከተማ ከስደስት ክልሎች አማራ፣ ኦሮምያ፣ ደቡብ ክልል፣ ሲዳማ፣ ሐረሪ፣ ከጤና ሚኒስቴር ተጠሪ ተቋማትና ከመድኃኒትና ፈንድ አቅርቦት ኤጀንሲ፣ ከኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት፣ ከአሐሪ፣ ከልማት አጋር ድርጅቶች፣ ከፌደራል ጤና ሚኒስቴር የወባ ማስወገድ ቡድን ኃላፊዎችና ባለሙያዎች በተገኙበት መካሄዱን ከሚኒስቴሩ ያገኘኘው መረጃ ያመላክታል።