Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

የመንግስት እና ፓርቲ መደበላለቅ በቅድመ ምርጫ ወቅት የቀደሞውን ኢ-ፍትሃዊነት እንዳያነግስ ሊታሰብበት ይገባል – የፖለቲካ ፓርቲዎች

አዲስ አበባ፣ የካቲት 17፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የመንግስት እና ፓርቲ መደበላለቅ በቅድመ ምርጫ ወቅት የቀደሞውን ኢ-ፍትሃዊነት እንዳያነግስ ሊታሰብበት እንደሚገባ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጠይቀዋል።

ከፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ጋር ቆይታ ያደረጉ የእናት ፓርቲ እና የህብር ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ አመራሮች፥ አሁንም የፓርቲ እና መንግስት ሚና መደበላለቅ ልጓም ካልተበጀለት 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ፍትሃዊነት ጥያቄ ውስጥ መውደቁ አይቀርም ብለዋል።

የመገናኛ ብዙሃንም ሆነ የመንግስት ተቋማት ከገዥው ፓርቲ ጋር የሙጥኝ ብሎ የመጣበቅ አባዜያቸውን ትተው በፍትሃዊነት እንዲያገለግሉም ነው ፓርቲዎቹ የጠየቁት፡፡

የፍትሀዊነት ጉዳይ በምርጫ ቅስቀሳም ሆነ በክርክሩ ወቅት ሊታሰብበት እንደሚገባም አንስተዋል።

ተፎካካሪ ፓርቲዎችም ስም ከማጥፋት እና ማጠልሸት ያረጀ አካሄድ ወጥተው የሰለጠነ ክርክር በማድረግ መራጩ ህዝብ በእውቀት ላይ ተመስርቶ እንዲመርጥ እድል ሊሰጡት ይገባል ባይ ናቸው፡፡

ምርጫ ማካሄድ የሀገርን መፃኢ እድል የመወሰን ሀይሉ ከፍተኛ መሆኑን የጠቆሙት የፓርቲዎቹ አመራሮች፤ ከዚህ ቀደም የነበሩ ደም መፋሰሶች ሳይመጡ ሀገሪቱን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር ፓርቲዎች ከስልጣን እሽቅድምድሙ በፊት የሀገር ህልውናን ሊያስቀድሙ እንደሚገባ ተናግረዋል ፡፡

በፋሲካው ታደሰ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡-

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

Exit mobile version