አዲስ አበባ፣ መስከረም 4፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በኦሮሚያና በደቡብ ክልሎች ከትምህርት ገበታቸዉ ርቀዉ ያሉ ተማሪዎችን ለመመለስ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ምክክር እየተደረገ መሆኑ ተገለፀ።
በምክክር መድረኩ “ኢማጅን ዋን ዴይ” የተሰኘ ዓለም አቀፍ ግብረ ሠናይ ድርጅት ÷ በተለያዩ ምክንያቶች በኦሮሚያና በደቡብ ክልሎች ከትምህርት ገበታቸው የተፈናቀሉ ከ21 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ወደ ትምህርት ገበታቸዉ ለመመለስ በሚደረገው ጥረት የጎላ ሚና እንደነበረው የትምህርት ሚኒስቴር ዴኤታዉ ዶክተር ገረመዉ ሁሉቃ ገልጸዋል።
ግብረ-ሠናይ ድርጅቱ ÷ በ “ቤቴ” በተሰኘ ፕሮጀክት በኦሮሚያ ክልል 6 ዞኖች ማለትም በምስራቅ ባሌ፣ ባሌ፣ በጉጂ፣በምእራብ ጉጂ፣ በም/ወለጋ፣ በም/እራብ ወለጋ እና በ10 ወረዳዎች ዉስጥ 15 ሺህ 25 ህጻናት እንዲሁም በደቡብ ክልል በኮንሶ ዞን በ 3 ወረዳዎች የሚገኙ 6 ሺህ 750 ህጻናት በጥቅሉ በሁለቱ ክልሎች የሚገኙ 21 ሺህ 775 ህጻናትን ወደ ትምህርት ለመመለስ እየሠራ መሆኑ ነው የተመላከተው።
የ “ቤቴ” ፕሮጀከት በ “ኢማጅን ዋን ዴይ” ግብረ ሠናይ ድርጅት የሚተገበር ሲሆን ለዚህ ስራ ከ80 ሚሊየን ብር በላይ ድርጅቱ መመደቡን ገልጿል።
የ “ቤቴ” ፕሮጀክት ለ10 ወራት ተግባራዊ የሚደረግ መሆኑንም ኦ ቢኤን ዘግቧል።