Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በሚያቀርበው የትኛውም አጀንዳና የትኛውም ተወያይ ጋር መንግስት ለምክክር ዝግጁ መሆኑን አረጋገጡ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 27፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በሚያቀርበው የትኛውም አጀንዳና ከሚያቀርበው የትኛውም ተወያይ ጋር መንግስት ለምክክር ዝግጁ መሆኑን አረጋገጡ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፥ ከአገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ አመራርና አባላት ጋር ተወያይተዋል።

በውይይቱም የአገራዊ የምክክር ኮሚሽን ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ፥ ኮሚሽኑ ባለፉት አራት ወራት ባከናወናቸው ተግብራት ዙሪያ ገለፃ አድርገዋል።

ኮሚሽኑ በቅድመ ዝግጅት ምዕራፍ የተለያዩ ተግባራትን ማከናወን እንደቻለም አስረድተዋል።

በውይይቱ ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደተናገሩት፥ አገራዊ ምክክሩ በዜጎቿ ተሳትፎ የተሻለች ኢትዮጵያን በመገንባት ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ ትልቅ ዕድል የሚፈጥር ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ፥ መንግስት የምክክር ኮሚሽኑን በሚያስፈልገው ነገር ሁሉ እንደሚደግፍ አስታውቀዋል ።

በኮሚሽኑ ስራ ላይ ምንም አይነት ጣልቃ ገብነት ሊኖር እንደማይችልም አረጋግጠዋል ።

ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በሚያቀርበው የትኛውም አጀንዳ እና ከሚያቀርበው ከየትኛውም ተወያይ ጋር መንግስታቸው ለምክክር ዝግጁ እንደሆነም ነው ያረጋገጡት።

በአልአዛር ታደለ

Exit mobile version