Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

የኦሮሚያ ብልጽግና ፓርቲ በክልሉ ለተደረገው የድጋፍ ሰልፍ ምስጋና አቀረበ

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 24፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የኦሮሚያ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት በክልሉ ከለውጡ በኋላ የተገኘውን ድልና ስኬት ለማስቀጠል ለተደረገው የድጋፍ ሰልፍ ምስጋና አቅርቧል፡፡

የቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ ፈቃዱ ተሰማ÷ ከለውጡ በኋላ የተገኘውን ድልና ስኬት ለማስቀጠል በክልሉ ዛሬ የተካሄደውን የድጋፍ ሰልፍ አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

በመግለጫቸውም÷በኦሮሚያ ክልል ሀሉም አካባቢዎች በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎች በነቂስ ወጥተው ለለውጡ ያላቸውን ድጋፍ መግለጻቸውን አንስተዋል፡፡

የድጋፍ ሰልፉ ተሳታፊዎች ለነጻነት፣ ለእኩልነትና ለፍትህ ለተካሄደው ትግል እንዲሁም ከለውጡ በኋላ ለተመዘገቡት ድሎች እና ስኬቶች እውቅና ሰጥተዋል ነው ያሉት፡፡

የሰልፉ ተሳታፊዎች በሰላማዊ መንገድ የመጣውን ለውጥ በሴራና በሃይል ለማደናቀፍ የሚንቀሳቀሱ ጽንፈኞች ሃይሎችን እንደሚታገሉ ጠንካራ መልዕክት አስተላልፈዋልም ብለዋል፡፡

በድጋፍ ሰልፉ ለተሳተፉ የሃገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ አባ ገዳዎች፣ የሲንቄ እናቶች፣ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ አርሶ አደሮች፣ የመንግስት ሰራተኞች እና ለሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ምስጋና አቅርበዋል፡፡

አቶ ፈቃዱ የድጋፍ ሰልፉ በስኬት እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን ሚና ለተውጡ የጽጥታ አካላት እና የመንግስት አመራሮችንም አመስግነዋል፡፡

Exit mobile version