Site icon Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C

ጠ/ሚ ዐቢይ ያገኙት የኖቤል የሰላም ሽልማት ሜዳሊያና ዲፕሎማ ቅጂ በሰላም ሚኒስቴር ተቀመጠ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 5፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ካገኙት የኖቤል የሰላም ሽልማት ሜዳሊያና ዲፕሎማ ቅጂ ለህዝብ ተደራሽ እንዲሆን በሰላም ሚኒስቴር ተቀመጠ።

የኢፌዴሪ የሰላም ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚልን ጨምሮ የሚኒስቴሩ ከፍተኛ አመራሮችና ሰራተኞች፣ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ተጠሪ ተቋማት ከፍተኛ አመራሮችና ሰራተኞች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሀይማኖት መሪዎች እንዲሁም ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው ባለድርሻ አካላት በተገኙበት የማስቀመጥ ስነ ስርዓቱ ተከናውኗል።

ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተበረከተላቸው ስጦታዎች ቅጂ ለህዝብ ተደራሽ ለማድረግ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ መመረጡም ነው በስነ ስርዓቱ ላይ የተነገረው።

ይህ የሀገር ልዩ ስጦታ በክብር እንዲቀመጥ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ መመረጡ ለቀጣይ ሀገራዊ ብሎም አህጉራዊ የሰላም ስራዎችን መስሪያ ቤቱ እንዲሰራ የሚያበራታታ መሆኑን ነው የሰላም ሚኒስትሯ ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል የተናገሩት።

ተምሳሌትነቱ፣ ተደራሽነቱ እና ቱርፋቱ ለመላው የሀገሪቱ፣ የአህጉሪቱ እንዲሁም ለመላው ሰላም ወዳድ የዓለም ማህበረሰብ መሆኑንም ገልፀዋል።

በቅድስት ተስፋዬ

Exit mobile version