Fana: At a Speed of Life!

ለሥራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት መስጠት እንደሚገባ ቋሚ ኮሚቴው አሳሰበ

አዲስ አበባ፣ የካቲት 4፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሃብት ልማት፣ ስራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኪሚቴ የሥራ እና ክህሎት ሚኒስቴር ለስራ ዕድል ፈጠራው ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንዳለበት አስገነዘበ፡፡
የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ዶክተር ነገሌንጮ እንደገለጹት÷ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ለአገራችን ኢኮኖሚ ዕድገት ሚናው ከፍተኛ በመሆኑ ተፈላጊውን ዕድገት ለማምጣት የሥራ ዕድል ፈጠራው የማይተካ ሚና ስላለው አፈጻጸሙን ፍትሃዊ ማድረግ ይገባዋል ብለዋል፡፡

ከለጋሽ ሃገራት የሚገኙ እርዳታና ብድሮች በተገቢው መንገድ ለስራ ዕድል ፈጠራ ዓለማ መዋላቸውን ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ መከታተል እንዳለበትም አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው አባላት በበኩላቸው ፥ የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል፣ የገበያ ትስስር በመፍጠርና የቴክኖሎጂ ሽግግር በማድረግ ሥራ አጥነትን መቅረፍ እንደሚቻል አመላክተዋል፡፡

ከብድር አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የሚታዩ ብልሹ አሰራሮችን በማስወገድ የዜጎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚቻልም ጠቁመዋል፡፡

የሥራ እና ክህሎት ሚኒስትር ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል ፥ 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ታቅዶ ከ1 ሚሊየን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፈጠሩን ለቋሚ ኮሚቴው አስረድተዋል፡፡

ከመሻገር ይልቅ መቆየት የሚፈልጉ ኢንተርፕራይዞች በመኖራቸው የአሰራር ስርዓት በመዘርጋት ተጠያቂነትን ጭምር በማረጋገጥ ለሌሎች አዳዲስ ስራ አጥ ዜጎች እድሉን እንዲሰጡ ለማድረግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመወያየት መፍትሄ የሚሰጥ መሆኑን አመላክተዋል፡፡

በአገልግሎት ዘርፉ ለብዙ ዜጎች የስራ እድል ቢፈጠርም በሌሎች በቱሪዝም እና በግብርና ዘርፎች የስራ እድል ለመፍጠር ከክልሎችና ከሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች ጋር በጥናት ላይ የተመረኮዘ ስራ ለመስራት ዕቅድ መያዙን ሚኒስትሯ ማስረዳታቸውን ከምክር ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

ኢትዮጵያን፦ እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.