“ለኢትዮጵያ እንቁም” የተሰኘ ዘመቻ በለንደን ተካሄደ
አዲስ አበባ ፣ የካቲት 23 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ለንደን በተከበረው 126ኛው የዓድዋ ድል በዓል የመታሰቢያ መርሃ-ግብር ላይ “ለኢትዮጵያ እንቁም” የተሰኘ ዘመቻ ተካሄደ፡፡
የኢትዮጵያ የዓለም ፌዴሬሽን የተሰኘ የጥቁሮች ህዝቦች የሆነ ድርጅት ዘመቻውን መምራቱን በለንደን የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመላክታል፡፡
በለንደን የኢፌዴሪ አምባሳደር ተፈሪ መለስ በመርሃ-ግብሩ ላይ የተገኙ ሲሆን ይህን ሠናይ ተግባር ላዘጋጁ አካላት ልባዊ ምሥጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
አምባሳደሩ የዓድዋ ድል በዓል ለኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካውያን ነጻነትም የላቀ ሥፍራ አለው ብለዋል፡፡
በዓድዋ ድል በዓል የመታሰቢያ መርሃ-ግብር ላይ የተለያዩ ማኅበረሰቦችን የሚወክሉ ቡድኖች፣ ድርጅቶች እና በዩናይትድ ኪንግደም የራስ ተፈሪያን ንቅናቄ አባላት ተገኝተዋል፡፡