Fana: At a Speed of Life!

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የኢትዮጵያ እና የሶማሊያ ግንኙነት ይበልጥ እንደሚጠናከር ያላቸውን እምነት  ገለጹ

አዲስ አበባ ፣ ሰኔ 2 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ኢትዮጵያና ሶማሊያ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ይበልጥ እንደሚያጠናክሩ ያላቸውን እምነት ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአዲሱ የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼህ ማህሙድ በዓለ ሲመት ላይ በሞቃዲሾ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፥ በሶማሊያ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር በመደረጉ መደሰታቸውን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የጋራ እድገት እና ልማት ትብብር ላይ የተመሰረተ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ በመከተሏ ሁለቱ አገሮች በቀጣናዊ ትስስር አዲስ መንገድ መክፈታቸውን ተናግረዋል።

ባለፉት ጥቂት ዓመታት  የተገኙ ዲፕሎማሲያዊ ድሎች ከአዲሱ  የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ጋር በጋራ በመስራት ይበልጥ እንደሚጠናከሩ እና እንደሚሰፉም ነው ያስታወቁት።

በኢትዮጵያ በሶማሊያ መካከል ያለው ግንኙነት የበለጠ እንዲጠናከር በኢትዮጵያ መንግስት በኩል አስፈላጊው ጥረት እንደሚደረግም አረጋግጠዋል።

አዲሱ የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ ማህሙድ ስራቸው የተሳካ ይሆን ዘንድ ኢትዮጵያ አስፈላጊውን ትብብርና ድጋፍ እንደምታደርግም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ  አስታውቀዋል።

ያለጎረቤቶቻችን ትብብርና ድጋፍ በተናጠል ሰላምና ልማትን ማረጋገጥ አንችልም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፥ ኢትዮጵያና  ሶማሊያ   የጋራ ባህላቸውን፣ ደህንነታቸውንና  ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን በማጠናከር  ብልጽግናን እንደሚያረጋግጡም ጠቁመዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በዚሁ ንግግራቸው፥ ለፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ ማህሙድ የተሳካ የስራ ዘመን እንዲሆንላቸውም ተመኝተዋል።

ፕሬዚዳንት ሀሰን ሼክ ማህሙድ በበኩላቸው በኢኮኖሚ ጠንካራ እና ሰላሟ የተረጋገጠ ሶማሊያን ለመፍጠር እንሰራለን ብለዋል።

“ከአፍሪካ ቀንድ ሀገራትና ከመላው አለም ጋር ጠንካራ ትብብር እንመሰርታለን” ያሉት ፕሬዚዳንቱ፥ የትብብር መስኮችም ንግድ፣ ኢኮኖሚና ሽብርተኝነትን መዋጋት እንደሚሆንም አስታውቀዋል።

በአልአዛር ታደለ

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.