Fana: At a Speed of Life!

አቶ ሽመልስ አብዲሳ በሮቤ ከተማ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን መረቁ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 22፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ በሮቤ ከተማ ተገንብተው የተጠናቀቁ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን መረቁ።
ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ፣ የተባባሩት አረብ ኤምሬቶች ዓለም አቀፍ ቀይ ጨረቃ እርዳታ ድርጅት ምክትል ዋና ፀሐፊ ፈህድ አብዱራህማን ቢን ሱልጣን እና የክልሉ ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች፥ በመንግስት፣ በሕዝብ እና አጋር አካላት የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶችን በጋራ በመመረቅ ስራ አስጀምረዋል።
በዛሬው ዕለት ከተመረቁ ፕሮጀክቶች መካከል፥ በሮቤ ከተማ በ41 ሚሊየን ብር ወጪ የተገነባው ጀነራል ዋቆ ጉቱ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ይገኝበታል፡፡
ትምህርት ቤቱ 24 የመማሪያ ክፍሎች፣ ቤተ ሙከራ እና ቤተ መጻሕፍት እንዲሁም ሁለት የአስተዳዳር ሕንጻዎችን ያካተተ መሆኑ ተገልጿል፡፡
ከ3 ሺህ 500 በላይ ተማሪዎችን በሁለት ፈረቃ ማስተማር እንደሚችልም ነው የተመላከተው፡፡
በተመሳሳይ ዛሬ ከተመረቁት የልማት ፕሮጀክቶች አንዱ፥ በ40 ሚሊየን ብር በሮቤ ከተማ የተገነባው የእናቶች እና ሕጻናት ሆስፒታል ነው።
ሆስፒታሉ፥ የእናቶች ማዋለጃ፣ የጨቅላ ሕጻናት፣ የማህፀን ክትትል እና የሕጻናት ክትባት፣ ሦስት የቀዶ ህክምና ክፍሎችን፣ ላቦራቶሪ እና ፋርማሲን ያካተተ ነው፡፡
በተጨማሪም 32 የእናቶች እና 12 የሕጻናት አልጋዎች እንዳሉትም ነው የተገለጸው፡፡
ከግንባታው ወጪ በተጨማሪ በተባባሩት አረብ ኤምሬቶች ዓለም አቀፍ ቀይ ጨረቃ እርዳት ድርጅት ሙሉ ዘመናዊ የህክምና መሳሪያ ተሟልቶለታል።

የአብዲ ቦሩ የሕጻናት ትምህርት ቤት ዛሬ ከተመረቁት የልማት ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ ሲሆን÷ በ412 ነጥብ 9 ሺህ የአሜሪካን ዶላር ወጪ የተገነባ ነው፡፡

ትምህርተ ቤቱ 6 ብሎኮች ያሉት ሲሆን÷ 333 ሕጻናትን ተቀብሎ የማስተማር አቅም እንዳለው ተገልጿል፡፡

በዛሬው ዕለት ከተመረቁት ፕሮጀክቶች በ1 ነጥብ 6 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር ወጪ የተገነባው የመደ ወላቡ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አንዱ ሲሆን÷ 24 ክፍሎች ያሉት እና 2 ሺህ 200 ተማሪዎችን የማስተማር አቅም እንዳለው ተገልጿል፡፡

 

በተመሳሳይ በ21ሚሊየን ብር የተገነባው የጀነራል ዋቆ ጉቱን ሐውልት የያዘው አደባባይ ተመርቋል።

ባለፉት ዓመታት ለበርካታ ጊዜ  የባሌ ሕዝብ የእኚህን ጀግና መሪ የሚዘክር ሐውልት እንዲሠራ ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ ሳያገኝ ቆይቷል።

ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ “ጀነራል ዋቆ በተከተሉት መርህ መሠረት ዛሬ በልጆቻቸው ሐውልታቸው ቆሞ ተስፋቸውም በልማታቸው እየተመለሰ ይገኛል” ብለዋል።

 

በበላይ ተስፋዬ
ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.