Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያ ለድህረ ግጭት ማገገሚያ የሚውል ወሳኝ የሚባል የፋይናንስ ድጋፍ እንዲደረግላት ጠየቀች

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 1፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ)  በኢትዮጵያ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል የተከሰተውን ግጭት ተከትሎ ከገጠማት ቀላል የማይባል ኪሳራ ለመውጣት እና ለመልሶ ግንባታ ዓለም ባንክና ሌሎች አጋር አካላት ድጋፍ እንዲያደርጉ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚንስትር አቶ ደመቀ መኮንን ጠየቁ

በሴኔጋል በተካሄደው የዓለም ባንክ ዓለም አቀፍ የልማት ማህበር (IDA20) የመሪዎች ጉባኤ ላይ የተካፈሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚንስትር አቶ ደመቀ መኮንን ባደረጉት ንግግር፥ የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ የተከሰተውን ግጭት ተከትሎ አጣዳፊ ጥናትና ግምገማ በማድረግ በግጭቱ ለተጎዱ አካባቢዎች ስለሚያስፈልጋቸው ድጋፍ ልየታ አድርጎ በማሳወቁ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ ከ2018 ጀምሮ እያደረገችው ላለው አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ድጋፍ የሚውል የ1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር መመደቡም የሚደነቅ መሆኑን አመልክተዋል፡፡

እንደ አጠቃላይ አፍሪካ ካለችበት ችግር እንድትወጣና የተሻለ ልማት እና መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር እንድታስመዘግብ ካስፈለገ ወሳኝ የሚባል የፋይናንስ ድጋፍ እንዲደረግላትም ነው አቶ ደመቀ ጥሪ ያቀረቡት።

የዓለም ባንክ ዓለም አቀፍ የልማት ማህበር (IDA20) ፕሮግራም በመሪዎቹ መድረክ ላይ አፍሪካ እንደ አየር ንብረት ለውጥ እና ኮቪድ 19 ፣ የዩክሬኑ ጦርነት ያመጣውን ዳፋ እና የተከሰተውን የምግብ ዋስትና ችግር ያሉ መሰናክሎችን መቋቋም የሚያስችል ድጋፍ እንደሚያደርግም ቃል ገብቷል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን የመሩት የኢትዮጵያ ልዑክ የብሔራዊ ባንክ ገዥ ዶክተር ይናገር ደሴ እና የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማክሮኢኮኖሚ አማካሪ አቶ ተክለወልድ አጥናፉን ያካተተ መሆኑን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.