Fana: At a Speed of Life!

ፋሲል ከነማ እና ድሬዳዋ ከተማ የቅጣት ውሳኔ ተላለፈባቸው

አዲስ አበባ፣ሐምሌ 4፣2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየርሊግ ተሳታፊዎች ፋሲል ከነማ እና ድሬዳዋ ከተማ እግር ኳስ ክለቦች  የሥነ ምግባር ቅጣት ውሳኔ ተላልፎባቸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር አመራርና ስነ-ስርዓት ኮሚቴ ባደረገው ስብሰባ በተደረጉ የፕሪሚየር ሊግ ውደድሮች ከዳኞች እና ከታዛቢዎች የቀረቡለትን የዲሲፕሊን ሪፖርት በመመርመር የተለያዩ የዲሲፕሊን ውሳኔዎችን አስተላልፏል።

በዚህ መሰረትም ድሬዳዋ ከተማ ከባህርዳር ጋር በነበረው የ28ኛ ሳምንት እግር ኳስ ጨዋታ ውድድሩ ከተጠናቀቀ በኋላ የክለቡ ደጋፊዎችና የቡድን አመራሮች አፀያፊ ስደብ ስለመሳደባቸው ሪፖርት ቀርቦበታል፡፡

የክለቡ ደጋፊዎችና የቡድን አመራሮች በዕለቱ ባጠፉት ጥፋትና ከዚህ በፊት በተመሳሳይ ጥፋት ከተላለፈባቸው  ቅጣት ሊታረሙ ባለመቻላቸው ክለቡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን መመሪያ መሰረት 75 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንዲከፍል በሊግ ኩባንያው ዲስፕሊን ኮሚቴ ተወስኖበታል፡፡

በተመሳሳይ ፋሲል ከነማ እግር ኳስ ቡድን ከድሬዳዋ ከተማ ጋር በነበረው የ30ኛ ሳምንት እግርኳስ ጨዋታ ከ68ኛው ደቂቃ ጀምሮ ስፖርታዊ ጨዋነትን ያልተከተለ ድጋፍ ስለመስጠቱ ሪፖርት ቀርቧል፡፡

በተጨማሪም ጨዋታው ከተጠናቀቀ በኋላ የጥበቃ ሃይሎች ሊቆጣጠሩት ባልቻለ ሁኔታ የክለቡ ደጋፊዎች ወደ መጫወቻ ሜዳ ጥሰው ስለመግባታቸውና ስለማወካቸው እንዲሁም ለሜዳሊያ አሰጣጥ ስነስርዓት አፈጻጸም እንቅፋት ስለመሆናቸው በሪፖርቱ ተመላክቷል።

በዚህም የክለቡ ደጋፊዎች በዕለቱ ባጠፉት ጥፋትና ከዚህ በፊት በተመሳሳይ ጥፋት ከተላለፈባቸው ቅጣት ሊታረሙ ባለመቻላቸው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን መመሪያ መሰረት 100 ሺ ብር እንዲቀጡ ተወስኖባቸዋል፡፡

በተጨማሪም ፋሲል ከነማ  በሜዳውየሚያደርጋቸውን ሁለት ጨዋታዎች ያለደጋፊ በዝግ ስታዲየም እንዲያካሂድ መወሰኑን ከሊግ ኩባንያው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.