Fana: At a Speed of Life!

በአንዳንድ አካባቢዎች ቅጽበታዊ ጎርፍ ሊያስከትል የሚችል ከባድ ዝናብ ሊኖር ስለሚችል ህብረተሰቡ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ተጠየቀ

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 6፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በመጠንም ሆነ በስርጭት ብዙ አካባቢዎችን የሚሸፍን እርጥበት እንደሚኖር እና በአንዳንድ አካባቢዎች ቅጽበታዊ ጎርፍ ሊያስከትል የሚችል ከባድ ዝናብ ሊኖር ስለሚችል ህብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ ብሔራዊ የሚቲዮሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስጠነቀቀ፡፡

ባለፉት ቀናት በተከታታይ ዝናብ እያገኙ ያሉና ውሃ የመሸከም አቅማቸው ከፍተኛ የሆነ የአፈር አይነት ያላቸው አካባቢዎች የአፈር ውስጥ እርጥበት መብዛት እንዲሁም ለጎርፍ ተጋላጭ በሆኑ ቦታዎች ከአፈር መሸርሸርም ሆነ ከመሬት መንሸራተት ጋር የተያያዙ ችግሮች ሊከሰቱ ስለሚችሉ ህብረተሰቡ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል፡፡

ከእርጥበት መብዛት ጋር ተያይዞ የአረም መጨመር ሊከሰት ስለሚችል አርሶ አደሩ አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርግም ተጠይቋል፡፡

በአንጻሩ በአርብቶ አደርና ከፊል አርብቶ አደር አካባቢዎች የሚጠበቀው እርጥበት በተለይም ባሳለፍናቸው ቀናት አካባቢዎቹ ካገኙት የተሻለ እርጥበት ጋር ተዳምሮ የመጠጥ ውሀ አቅርቦትና የግጦሽ ሳር ልምላሜ ከማሻሻል አንጻር ጥሩ ጎን እንደሚኖረው የኢንስቲትዩቱ መረጃ ያመላክታል፡፡

በአጠቃላይ ከላይ በትንበያው ላይ በተጠቀሱት አካባቢዎች በአብዛኛው ከመደበኛና ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ የሚያገኙ ሲሆን÷ ይህም የአፈር ውስጥ እርጥበትን ከማሻሻል አንፃር አስቀድመው የተዘሩና በተለያየ የዕድገት ደረጃ ላይ ለሚገኙ የበልግም ሆነ የመኸር ሰብሎች እንዲሁም ለተለያዩ የቋሚ ተክሎችና የጓሮ አትክልቶች የውሀ ፍላጎታቸውን ከማሟላት አንፃር ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ነው ያለው፡፡

ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.