Fana: At a Speed of Life!

ኢዜማ ለሀገራዊ ምክክሩ ስኬታማነት የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ ገለጸ

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 11 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ለሀገራዊ ምክክሩ ስኬታማነት የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ ገለጸ፡፡

ፓርቲው አዲስ የመረጣቸውን 21 የብሔራዊ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ዛሬ በሰጠው መግለጫ ይፋ አድርጓል፡፡

በዚህም መሰረት ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የፓርቲው መሪ፣ አርክቴክት ዮሐንስ መኮንን ምክትል መሪ፣ ዶክተር ጫኔ ከበደ ሊቀመንበር፣ አቶ አበበ አካሉ ዋና ጸሐፊ እና አቶ አንድነት ሽፈራው የፋይናንስ ሃላፊ በመሆን በጉባኤ መመረጣቸው ተገልጿል።

የፓርቲው ዋና ፀሐፊ አቶ አበበ አካሉ በዚሁ ወቅት የፓርቲው አመራሮችና አባላት ለሀገራዊ ምክክሩ ስኬታማነት የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

ሀገራዊ ምክክሩ የሀገሪቱን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመቅረፍ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ጠቅሰው ከዚህ አኳያ  ኢዜማ ለምክክሩ መሳካት በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

የፓርቲው ሊቀመንበር ዶክተር ጫኔ ከበደ በበኩላቸው ፓርቲውን በእውቀትና በክህሎት የሚመራ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት መመረጣቸውን ተናግረዋል።

ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላቱም የ100 ቀናት ዕቅድ አውጥተው ወደ ስራ እንደሚገቡ ማንሳታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡የፓርቲው መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ፤ ኢዜማ የፓርቲ ውስጠ ዴሞክራሲ ለምምድን በማጠናከር በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ስርዓት እንዲጎለብት የበኩሉን ሚና እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.