Fana: At a Speed of Life!

በህገወጥ መንገድ ሲዘዋወሩ የነበሩ ከ257 ሺህ በላይ የተለያዩ የውጭ ሃገራት ገንዘቦችና 6 ኪሎ ወርቅ ተያዙ

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 14፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በህገወጥ መንገድ ሲዘዋወሩ የነበሩ ከ257 ሺህ በላይ የተለያዩ የውጭ ሃገራት ገንዘቦች ተያዙ፡፡

እንዲሁም 24 ሚሊየን 339 ሺህ 280 ብር የሚያወጣ ከ6 ኪሎ በላይ ወርቅ ተይዟል፡፡

ህገ ወጥ ገንዘቦቹ እና ወርቆቹ የተያዙት በትናንትናው ዕለት መነሻዉን አዲስ አበባ መድረሻዉን ደግሞ ምስራቅ ሐረርጌ ሐረር ከተማ ለማድረግ አስቦ በመኪና ሲዟዟር ቀረሳ ኬላ ላይ ነው ፡፡

በዚህም ሁለት አዘዋዋሪዎች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርጓል፡፡

በህገ ወጥ መንገድ ሲዘዋወር የተያዘው ገንዘብም 182 ሺህ 675 የአሜሪካ ዶላር ፣ 5 ሺህ 530 የካናዳ ዶላር ፣ 1 ሺህ 800 ፓዉንድ እና 67 ሺህ 145 የሳኡዲ ሪያል መሆኑ ታውቋል፡፡

 

በሌላ በኩል በደቡብ ወሎ ዞን ኩታበር ወረዳ 250 የከባድ መሳሪያ ተተኳሾች መገኘታቸውን የወረዳው ሚሊሻ ጽ/ቤት ገልጿል።

የወረዳው ሚሊሻ ጽ/ቤት እንደገለጸው፥ በወረዳው 03 ቀበሌ ልዩ ስሙ አላንሻ ከተባለ ቦታ የተለያዩ የዙ-23፣ የዲሽቃና የሞርታር ተተኳሾች ተገኝተዋል።

የጽ/ቤቱ ኃላፊ አስር አለቃ ጸጋየ አባተ እንደገለጹት፥ የተገኙት የጦር መሳሪያ ዓይነቶች 130 የዲሽቃ ተተኳሽ ጥይት 97 የዙ 23 ተተኳሽ ጥይትና 13 የሞርታር ተተኳሽ ጥይት በአጠቃላይ 250 ተተኳሽ ጥይቶችና 3 የሞርታር ፊውዝ ናቸው።

መሳሪያዎቹ የትህነግ ወራሪ ቡድን ሲሸሽ ጥሏቸው የሄዱ እንደሆኑና በአካባቢው ማህበረሰብ ጥቆማ በፖሊስና የሚሊሻ ሃይሎች ክትትል ተደብቀው የተያዙና አንዳንዶቹም በግለሰብ ቤት የተገኙ መሆናቸውንም የኩታበር ወረዳ የመንግስት ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመለክታል።

የጦር መሳሪያዎቹ በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት ስለሚያስከትሉ ማህበረሰቡ ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበት ገልፀው፥ በጽ/ቤቱ በኩል ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን ክትትል እንደሚያደርግና ህብረተሰቡም ጥቆማ በመስጠት የተለመደ ትብብሩን እንዲቀጥል መልዕክት አስተላልፈዋል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.