Fana: At a Speed of Life!

ከ430 ሚሊየን ብር በላይ ካፒታል ካስመዘገቡ ኩባንያዎች ጋር ስምምነት ተፈረመ

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 13፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢንዱስትሪ ፓርኮች ኮርፖሬሽን ከ430 ሚሊየን ብር በላይ የኢንቨስትመንት ካፒታል ያስመዘገቡ ሦስት የሀገር ውስጥ ኩባንያዎች ጋር የውል ስምምነት ተፈራረመ፡፡

የውል ስምምነቱን የፈረሙት አፊያን የጨርቃጨርቅና አልባሳት ማምረቻ፣ አሊያኪም የምግብ ዘይት ፋብሪካና ዶሜን አልሙኒየም ኮምፖሲት ፓኔል የተሰኙ ኩባንዎች ናቸው።

የውል ስምምነቱ በኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሳንዶካን ደበበ እና በኩባንያዎቹ የሥራ ኃላፊዎች መካከል ተፈርሟል፡፡

የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሳንዶካን ደበበ በዚህ ወቅት እንዳሉት፥ መንግሥት አቅም ያላቸው የሀገር ውስጥ ባለሃብቶች በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ እንዲሰማሩ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል።

በተለይም የሀገር ውስጥ ባለሃብቶችን ለማበረታታት በተደረገው የአሰራር ማሻሻያ ባለፉት ሁለት ወራት ብቻ አራት ባለሃብቶች በፓርኮቹ ውስጥ በተለያዩ ዘርፎች እንዲሰማሩ የማግባባት ሥራ ተሰርቷል ብለዋል።

ስምምነቱ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ለባለሃብቱ ምቹ የሥራ ሁኔታን በመፍጠር ሀገሪቱ ከዘርፉ የምታገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ በአጭር ጊዜ ውስጥ እንድታገኝ ያግዛል ነው ያሉት።

በተጨማሪም ለበርካታ ዜጎች የሥራ እድል ከመፍጠር ባሻገር በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ የተለያዩ ምርቶችን ማምረትና ከሀገር ውስጥ አልፎ ለውጭ ገበያ ማቅረብ እንደሚቻል የሚያሳይ ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.