ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ሥራው ባሻገር በማኅበረሰብ ተኮር ሥራዎች የበለጠ መሥራት አለበት- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 5፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ሥራው ባሻገር በማኅበረሰብ ተኮር ሥራዎች የበለጠ መሥራት አለበት ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ተናገሩ፡፡
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲን ጎብኝተዋል፡፡
በጉብኝታቸውም÷ ዩኒቨርሲቲው ከአካዳሚክ ሥራው ጎን ለጎን ግቢዎቹን በአትክልትና ፍራፍሬ ለማስዋብ ያደረገውን ጥረት ተመልክተዋል።
ዩኒቨርሲቲው የጀመረው ተግባር ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ገልጸው÷ በሚያከናውነው የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሥራ ከራሱ አልፎ የአካባቢውን ማኅበረሰብ ተጠቃሚ ማድረግ እንዳለበት አስገንዝበዋል።
ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ሥራው ባሻገር በማኅበረሰብ ተኮር ሥራዎች የበለጠ መሥራት እንዳለበት መናገራቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡