በተደራጀ ሌብነትና ሙስና በተሳተፉ አካላት ላይ ሕጋዊ እርምጃ ይወስዳል – አቶ ኦርዲን በድሪ
አዲስ አበባ፣ ሕዳር 24፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የሐረሪ ክልል መንግሥት በተደራጀ ሌብነትና ሙስና በተሳተፉ አካላት ላይ ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለጹ።
ርዕሰ መስተዳድሩ 19ኛው የጸረ ሙስና ቀንን አስመልክቶ ባስተላለፉት መልዕክት÷ የክልሉ መንግሥት በሙስና ተግባር በተሳተፉ አካላት ላይ ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ ገልጸዋል።
ሙስና እና የተደራጀ ሌብነት ሕዝብን ያማረሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮች መሆናቸውን ጠቁመው÷ ሙስና ለመከላከል ሁሉም ዜጋ የድርሻውን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በሙስና እና የተደራጀ ሌብነት ላይ የተጀመረው ትግል ሁሉን አቀፍ መሆኑን ጠቅሰው÷ በመንግሥትም ይሁን በግሉ ዘርፍ በሙስና የተሳተፉ አካላት ላይ ያለርህራሄ እርምጃ እንደሚወሰድ አረጋግጠዋል፡፡
ህብረተሰቡ በየጊዜው በሙሰኞች ላይ አስተማሪ እርምጃ እንዲወሰድ ሲጠይቅ መቆየቱን አስታውሰው÷ በክልል ደረጃ የጸረ ሙስና ኮሚቴ መቋቋም ለሕዝብ ጥያቄው ምላሽ ይሰጣል ብለዋል፡፡
የጸረ ሙስና ትግሉ ተቋማዊ አደረጃጀትን በመያዝ ተጠናክሮ ይቀጥላል ማለታቸውን የክልሉ ኮሙኒኬሽን መረጃ አመላክቷል፡፡