Fana: At a Speed of Life!

በዓለም ዋንጫው ለሶስተኛ ጊዜ የተገናኙት አርጀንቲና እና ክሮሺያ ምሽት በግማሽ ፍጻሜው ይጫወታሉ

አዲስ አበባ፣ ታኅሣሥ 4፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በዓለም ዋንጫ የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ዛሬ ምሽት አንድ ጨዋታ ይደረጋል።

በግማሽ ፍጻሜው የመጀመሪያ ጨዋታ የሊዮኔል መሲዋ አርጀንቲና ከክሮሺያ ምሽት 4 ሰአት ጨዋታዋን ታደርጋለች።

አርጀንቲና በዓለም ዋንጫው ከክሮሺያ ጋር ሁለት ጊዜ በምድብ ድልድል ሲገናኙ በፈረንሳዩ የዓለም ዋንጫ አርጀንቲና 1 ለ 0 ስታሸንፍ፥ በ2018 የሩሲያው የዓለም ዋንጫ ደግሞ ክሮሺያ 3 ለ 0 አሸንፋለች።

ከዛ ባለፈ በወዳጅነት ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ተገናኝተው አንድ አንድ ጊዜ ሲሸናነፉ አንድ ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል።

ክሮሺያ በዓለም ዋንጫው የስድስት ጊዜ ተሳትፎ ስታደርግ አርጀንቲና በአንጻሩ በ18 የዓለም ዋንጫ ውድድሮች በመሳተፍ ሁለት ጊዜ ባለድል ሆናለች።

ክሮሺያ በታሪኳ ትልቁ ስኬቷ ለፍጻሜ የበቃችበት የ2018ቱ የዓለም ዋንጫ ሲሆን፥ ጨዋታው በፈረንሳይ 4 ለ 2 አሸናፊነት መጠናቀቁ ይታወሳል።

ዛሬ ምሽት ሁለቱ ቡድኖች በሚያደርጉት ጨዋታ አርጀንቲና በጠንካራ የቡድን መንፈስ በሊዮኔል መሲ ልዩነት ፈጣሪነት የምታደርገው እንቅስቃሴ ከወዲሁ ትኩረትን ስቧል።

በአንጻሩ ከኋላ ጠንካራ ደጀን ያላትና በሞድሪች፣ ኮቫችች እና ብሮዞቪች የሚመራው የክሮሺያ አማካይ ክፍል የሚያደርገው እንቅስቃሴም ተጠባቂ ነው።

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.