Fana: At a Speed of Life!

ምሁራን የመፍትሔ ሀሳብ በማፍለቅ በሀገረ-መንግሥት ግንባታ ላይ የመሪነት ሚናቸውን እንዲወጡ ተጠየቀ

አዲስ አበባ፣ ታኅሣሥ 13፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ምሁራን በእውቀት ላይ የተመሰረተ የመፍትሔ ሀሳብ በማፍለቅ በሀገረ-መንግሥት ግንባታ ላይ የመሪነት ሚናቸውን እንዲወጡ የሰላም ሚኒስቴር ጥሪ አቀረበ፡፡

“የሀገረ-መንግሥት ግንባታና የምሁራን ሚና” በሚል ርዕሰ ጉዳይ የዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች፣ የምርምር ተቋማት ኃላፊዎችና ሌሎች የሚመለከታቸውን አካላት ያካተተ ሀገራዊ የምሁራን የምክክር መድረክ ማስጀመሪያ መርሐ-ግብር ተካሂዷል፡፡

ከ400 ሺህ በላይ የዩኒቨርሲቲ፣ የኮሌጅና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መምህራንና ተመራማሪዎች፣ የምርምር ተቋማት ምሁራንና የሲቪል ማኅበረሰብ አባላት የሚሳተፉበት ሀገራዊ የምክክር መድረክ በቀጣይ ጊዜያት እንደሚካሄድም ተገልጿል፡፡

የሰላም ሚኒስትሩ ብናልፍ አንዷለም÷ ሀገራዊ የምክክር መድረኩ ምሁራን በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም ለማስፈንና የጋራ ጉዳዮችን ለማጉላት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።

ምሁራን ከመጠላለፍ የፖለቲካ እሳቤ ወጥተው በእውቀት ላይ የተመሰረተ የመፍትሔ ሀሳብ ማቅረብ አለባቸው ብለዋል፡፡

የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋበበኩላቸው÷ምሁራን ከቀደመው ትውልድ የተገኘውን ሁለንተናዊ ድል፣ ሰላምና ነፃነት በሙያቸው የማስቀጠል ኃላፊነት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።

 

ከአክራሪነትና ከብሔር አጥር ወጥተው ለሁሉም የምትመችና የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በተቋማዊ ግንባታ ላይ አዎንታዊ ሚናቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ÷ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የነፃነት ምልክት፣ የቀደምት ሥልጣኔ መገለጫና የአኩሪ ታሪክ ባለቤት በመሆኗ የሁላችንም ክብርና ኩራት ነው ብለዋል።

ምሁር ማለት የሕብረተሰቡን ችግር ተረድቶ በጥናት ላይ የተመሰረተ የመፍትሔ ሃሳብ የሚያቀርብ መሆኑን የገለጹት ደግሞ÷ የትምህርት ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋ ናቸው፡፡

ምሁራን የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲወጡ በመንግሥት በኩል አስፈላጊው ሁሉ እገዛና ድጋፍ እንዲደረግ ምሁራን መጠየቃቸውን ኢዜአ ዘግቧል።

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.