የገበታ ለሀገር ምዕራፍ ሁለት ማስጀመሪያ መርሐ ግብር ተካሄደ
አዲስ አበባ፣ የካቲት 5፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የገበታ ለሀገር ምዕራፍ ሁለት ማስጀመሪያ መርሐ ግብር የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በተገኙበት ተካሂዷል።
የገበታ ለሀገር ምዕራፍ ሁለት የሀብት ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብር በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ እስካሁን ተደራሽ ያልሆኑ ታላላቅ ሐገራዊ ፕሮጀክቶችን ለመገንባት የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል፡፡
የገበታ ለሐገር ምዕራፍ ሁለት የሐብት ማሰባሰቢያ የሀገር ውስጥ ባለሃብቶች አስተባባሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ÷በጋራ በመስራት እና በመትጋት የጀመርናቸውን ፕሮጀክቶን ጨርሰን-አሻራችን ለሚቀጥለው ትውልድ እናስቀምጣለን ብለዋል፡፡
ገበታ ለሐገር የተባበረ እጃችን የሚገነባው ፕሮጀክት ነው ማለታቸውን ከከተማ አስተዳደሩ ኮሙኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
በመድረኩ ባለሐብቶችና የመንግስት የስራ ሃላፊዎች የተገኙ ሲሆን÷1 ቢሊየን ብር ለማሰባሰብ ታቅዶ 1 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ቃል መገባቱ ተጠቁሟል፡፡