Fana: At a Speed of Life!

ከኢትዮጵያ የተዘረፉ 538 ያህል ቅርሶች በእንግሊዝ ተገኙ

አዲስ አበባ፣ የካቲት 28፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ከኢትዮጵያ የተዘረፉ በመቶዎች የሚቆጠሩ ባሕላዊ ቅርሶች በእንግሊዝ እንደሚገኙ ተገለጸ፡፡

ቅርሶቹ እንግሊዝ ኢትዮጵያን በፈረንጆቹ 1868 ላይ በወረረችበት ወቅት በወታደሮች መዘረፋቸውም ተጠቁሟል፡፡

“ዘ ፕሪንስ ኤንድ ዘ ፕላንደር” ወደ አማርኛ ሲመለስ “ልዑሉ እና ዘረፋው” የተሠኘ መፅሐፍ የደረሱት እንግሊዛዊው አንድሪው ሄቨንስ 538 ያህል የኢትዮጵያ ቅርሶች እንዴት ወደ እንግሊዝ እንደተወሰዱ በመፅሐፉ በዝርዝር አመላክተዋልም ነው የተባለው፡፡

ደራሲው ቅርሶቹ በለንደን እንደሚገኙ መጠቆማቸውንም ኤቭኒንግ ስታንዳርድ የተሰኘው የሀገሪቷ የዜና ምንጭ ዘግቧል።

የጠቀሷቸው ቅርሶች ከጥቃቅን እና ከተቀደሱ መፅሐፍት እና ቅርሶች ጀምሮ የከበሩ መዋቢያ የዕጅ አምባሮች ፣ የነገሥታት አልባሳት ፣ የነገሥታት የጋብቻ አልባሳት ፣ ዘውድ እና ታቦታት ይገኙበታል፡፡

የእንግሊዝ ወታደሮች ቅርሶቹን በያዟቸው ቦርሳዎች እና በኪሶቻቸው ይዘው መመለሳቸውንም ጠቁመዋል፡፡

ደራሲው ‘‘መፅሐፌ ቅርሶቹ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመለሱ የሚጠይቅ የቅስቀሳ መፅሐፍ አይደለም ፤ መረጃ ነው፡፡ መጠየቁ የኢትዮጵያ ጉዳይ ነው’’ ብለዋል፡፡

መረጃውን በመፅሐፋቸው ይፋ ያደረጉት አንድሪው ሄቨንስ ኢትዮጵያ ውስጥ በጋዜጠኝነት ይሰሩ እንደነበርም ተገልጿል፡፡

በዓለማየሁ ገረመው

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.